የብሔራዊ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን በአማራ ክልል ለድርቅ ተጎጂዎች የሚያደርገው የዕለት ደራሽ ዕርዳታ አቅርቦትን የሚያውክ የፀጥታ ችግር እስካሁን እንዳልገጠመው አስታወቀ፡፡
ባለፈው ሳምንት አማራ ክልልን ጨምሮ በድርቅ ወደ ተጎዱ ሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች የዕርዳታ ማሠራጨት ሥራ መጀመሩን ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡ በተለይ በአማራ ክልል በፋኖ ታጣቂዎችና በመንግሥት መካከል ውጊያ እየተካሄደ ቢሆንም፣ በግጭቱ ሳቢያ አቅርቦቱ አለመስተጓጎሉን ነው ኮሚሽኑ የገለጸው፡፡
ከዚህ ቀደም ኮሚሽኑ የውጭ ዕርዳታ ድርጅቶች ዕርዳታ በማቋረጣቸው ምክንያት ለ3.8 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ዕርዳታ ማቅረቡን፣ የኮሚሽኑ ከፍተኛ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ አታለል አቦሃይ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡
‹‹አማራ ክልልን ጨምሮ ድርቅ ወዳጠቃቸው ክልሎች አንድ ሚሊዮን ሊትር ዘይት፣ 54 ሺሕ ኩንታል አልሚ ምግብን ጨምሮ ከ610 ሺሕ ኩንታል በላይ የምግብ ዕርዳታ እንዲሠራጭ አድርገናል፤›› በማለት የተናገሩት አቶ አታለል፣ መንግሥት በራሱ አቅም አደጋውን ለመቋቋም እየሠራ ነው ብለዋል፡፡
በሰሜን ጎንደር ዞን አራት ወረዳዎችን ያጠቃው ድርቅ 86 ሺሕ ዜጎችን እንደጎዳ የጠቀሱት ኃላፊው፣ ለእነዚህ ወገኖች የሚሆን 14 ሺሕ ኩንታል ዕርዳታ ወደ ሥፍራው መላኩንም አክለዋል፡፡
በአማራ ክልል ያለው የወቅቱ የፀጥታ መደፍረስ የዕርዳታ አቅርቦቱን አስተጓጉሎት እንደሆነ የተጠየቁት አቶ አታለል፣ ‹‹በፀጥታ ችግር የተመለሰብን የዕርዳታ ተሽከርካሪ የለም፤›› ብለዋል፡፡
ኮሚሽኑ በድርቅ ለተጠቁና ሰብዓዊ ዕርዳታ ለሚሹ ወገኖች ፈጥኖ ከመድረስ ውጪ ሌላ የፖለቲካ ዓላማ እንደሌለው ተናግረው፣ ‹‹ለአማራ እታገላለሁ የሚል ወገን ለአማራ ክልል የሚቀርብ ዕርዳታን ካስተጓጎለ ወይም ከዘረፈ የሚታገልለት ዓላማ የሌለው መሆን አለበት፤›› በማለትም ገልጸዋል፡፡ እንደ እስካሁኑ ሁሉ የሰብዓዊ ረድዔቱ ሳይስተጓጎል ለተረጂዎች እንዲደርስ ሁሉም ወገን ትብብር እንዲያደርግም ጠይቀዋል፡፡