የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ተገቶ የተስፋ ጭላንጭል መታየት ሲጀምር፣ በአማራ ክልል ሌላ ዙር ዕልቂትና ውድመት ሊያደርስ የሚችል ግጭት መነሳቱ ብዙዎችን ያሳስባቸዋል፡፡ በአማራ ክልል የቀጠለውና ወራት ያስከተለው ግጭት ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳት እያስከተለ ሲሆን፣ በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ያለው ሁኔታም ከፍተኛ ሥጋት ያጠላበት ነው፡፡ እንደ ልብ ተንቀሳቅሶ መሥራትም ሆነ መዘዋወር በማይቻልበት ሁኔታ ውስጥ ያለችው ኢትዮጵያ፣ በኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በሥጋት የምትታይ አድርጓታል፡፡ ኢትዮጵያ በዚህ ሁኔታ መቀጠል ስለሌለባት መንግሥት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የሲቪል ማኅበረሰቦችና የአገር ጉዳይ የሚመለከታቸው ዜጎች በሙሉ ለሰላም መስፈን የጋራ ፍኖተ ካርታ ያስፈልጋቸዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በአማራ ክልል በበርካታ ሥፍራዎች እየተካሄደ ያለው ግጭት በፍጥነት ቆሞ ንግግርና ድርድር እንዲጀመር፣ መንግሥትም ሆነ ተገዳዳሪዎች ለሰላም መስፈን የሚበጁ ጉዳዮች ላይ ያተኩሩ፡፡ በግጭት ውስጥ ያሉ ኃይሎች የግጭትም ሆነ የጦርነት መጨረሻው ወደ ሰላም ጠረጴዛ ማምራት መሆኑን ይገንዘቡ፡፡
ለሁለት ዓመታት ያህል የተካሄደው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በዘመናችን ሰቅጣጭ የሚባል ነው፡፡ ከዕልቂት፣ ከውድመት፣ ከሰብዓዊ መብት ጥሰትና ከሚሊዮኖች መፈናቀል በኋላ በሰላም ስምምነት ቢገታም፣ በአገርና በሕዝብ ላይ ጥሎት ያለፈው ጠባሳ ግን ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ ነው፡፡ አውዳሚው ጦርነት ከመቀስቀሱ በፊት ለሰላም የተደረጉ ተደጋጋሚ ጥረቶች ባለመሳካታቸው፣ ኢትዮጵያ ከሩሲያና ከዩክሬን የባሰ ፍጅት የሚካሄድበት ጦርነት እያካሄደች እንደነበር በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ሳይቀር ሲዘገብ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ የመበታተን አደጋ እንደ ደረሰባቸው አገሮች በሥጋት እንድታይ ተደርጋለች፡፡ ያ አውዳሚ ጦርነት በሰላም ስምምነት ቆሞ አንፃራዊ ሰላም ሰፈነ ሲባል፣ ወዲያውኑ በአማራ ክልል በጣም አስፈሪ የሆነ ግጭት ተቀስቅሶ የንፁኃን ሞትና የንብረት ውድመት ሲከተል ለብዙዎች አስደንጋጭ ሆኗል፡፡ አሁንም ግጭቱ ተስፋፍቶ የበለጠ ጥፋት እንዳይደርስና የንፁኃን ሕይወት ለአደጋ እንዳይጋለጥ፣ በቅንነትና በስክነት በችግሩ መንስዔዎች ላይ በመነጋገር ለግጭቱ መቋጫ ለማግኘት ያላሰለሰ ጥረት ይደረግ፡፡ አሁን ባለው አስፈሪ ሁኔታ መቀጠል ስለማይቻል ለንግግር ቅድሚያ ይሰጥ፡፡
እስካሁን ድረስ ባለው የኢትዮጵያ የአገረ መንግሥት ግንባታ ታሪክ ውስጥ ጥቂት ልሂቃን ብቻ ጎልተው እየወጡ፣ ብዙኃኑ ሕዝብ አዳማጭ አጥቶ በእነሱ ዳፋ አሳሩን ሲያይ እንደነበር ከቶም አይዘነጋም፡፡ ብዙኃኑ ሕዝብ ከአገሩ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች እንዲገለል ተደርጎ፣ ጥቂቶች ሲስማሙ አንፃራዊ ሰላም እያገኘ ሲጣሉ ደግሞ መዓት እየወረደበት በመከራ ውስጥ መኖሩ የታወቀ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ልሂቃን አሠላለፋቸውን በየጊዜው እየቀያየሩ፣ ይህንን መከረኛ ሕዝብ ያለ ጥፋቱ የመከራ ቀንበር እየጫኑበት ነው፡፡ ይህ አደገኛና አልታረም ያለ የስህተት መንገድ ተለውጦ፣ ሁሉን አሳታፊና አካታች የሆነ አገራዊ የንግግርና የድርድር መድረክ መከፈት አለበት፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ፣ ጥምረት፣ ኅብረት፣ ግንባርና ሌላ የዳቦ ስም እየተሰጣጡ በሕዝብ ደም መነገድ መቆም ይኖርበታል፡፡ ለሥልጣን ሲባል በሚደረግ ትንቅንቅ ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ደሙንም ሆነ ሕይወቱን መገበር የለበትም፡፡ ይልቁንም በአገሩ ሁለንተናዊ ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ድምፁ መደመጥ አለበት፡፡
በተለያዩ አካባቢዎች የሚታዩ ግጭቶች በፍጥነት እንዲገቱና ወደ ሰላማዊ ንግግር መድረኩ ለመምጣት የሚያስችሉ ሕጋዊ ማዕቀፎች ያስፈልጋሉ፡፡ ሁሉም የግጭቱ ተዋናዮች፣ ዜጎች፣ በአገር አቀፍ ደረጃ አንቱታን ያተረፉ ታዋቂ የእምነት መሪዎች፣ የተከበሩ የአገር ሽማግሌዎችና ሌሎች አገር ወዳዶች ግጭቱ በፍጥነት ተገቶ በኢትዮጵያ አንፃራዊ ሰላም እንዲፈጠርና የሚፈለግባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ዕድሉ ይመቻች፡፡ በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ግጭት በመዘገብም ሆነ በፕሮፓጋንዳ ሥራ የተጠመዱ ወገኖችም፣ ግጭት አባባሽ ከሆኑ ድርጊቶች በመታቀብ በምድሪቱ ሰላም እንዲሰፍን የሚረዱ ተግባራትን በማከናወን ተባባሪ ይሁኑ፡፡ ሰላም ከሰፈነ የሚፈልጉትን ዓላማ ማሳካት የማይችሉ ወገኖች አንድ ልብ ሊሉት የሚገባ ጉዳይ አለ፡፡ እሱም ከእነሱ ዓላማ ወይም ጥቅም በላይ የአገር ሰላምና የሕዝብ ደኅንነት እንደሚቀድም መረዳት ነው፡፡ ከአገርና ከሕዝብ ህልውና በላይ የራሳቸውን ጥቅም በማስቀደም በሴረኝነት ንግግርና ድርድር እንዳይኖር እንቅፋት አይፍጠሩ፡፡ የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ያስከተለውን ዕልቂት፣ ውድመትና መፈናቀል በማስታወስ ከሰበብ ድርደራ ይውጡ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ዋናው ትኩረት መሆን ያለበት በአማራ ክልልም ሆነ በሌሎች አካባቢዎች፣ ግጭቶች በእኩልነትና በመከባበር መርህ ዕልባት እንዲያገኝ የሚረዳ ሥራ ብቻ ነው፡፡
እንደሚታወቀው በፀጥታ ችግር ምክንያት በተለያዩ አካባቢዎች የተመረቱ ምርቶችን ወደ ገበያ ማቅረብ አዳጋች እየሆነ ነው፡፡ ግጭቶች ባሉባቸው ሥፍራዎች ደግሞ ማምረት እየተቻለ አይደለም፡፡ ባለፈው ዓመት ማዳበሪያና የተለያዩ ግብዓቶችን በወቅቱ ማቅረብ ባለመቻሉና በተለያዩ ምክንያቶች፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚጠበቀው የመኸር ምርት መጠኑ ሊቀንስ እንደሚችል ይነገራል፡፡ በጣም መሠረታዊ የሚባሉ የምግብ ምርቶች ዋጋቸው ከመቼውም ጊዜ በላይ እየናረ ሲሆን፣ ከመኸር ምርት የሚጠበቀው መጠንም አነስተኛ ሊሆን ስለሚችል የዋጋ ንረቱ ማሻቀቡ አይቀሬ ነው፡፡ በዚህ ላይ ሰሞኑን የነዳጅ ዋጋ በመጨመሩ ምክንያት በምርቶች ዋጋ ላይ ጭማሪ እንደሚኖር ይጠበቃል፡፡ እነዚህና መሰል ችግሮች ሊፈቱ ባልቻሉበት ሁኔታ ውስጥ ግጭቶች እየተባባሱ ሲሄዱ ቀውሱም ይቀጥላል፡፡ ይህ ዓይነቱ አሳዛኝ መከራ ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንደማይገባው በመገንዘብ፣ መንግሥትን ጨምሮ ሁሉም አካላት የመጪውን ጊዜ አስፈሪነት ከግምት በማስገባት ለሰላማዊ መፍትሔ ይትጉ፡፡
ግጭቶች እየተባባሱ ሲሄዱ ከዚህ ቀደም ግጭቶች ከተካሄዱባቸው ሥፍራዎች የተፈናቀሉ ወገኖች ተጎጂ ሲሆኑም እየተስተዋለ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ፣ በሶማሌና በኦሮሚያ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢ በቅርቡ በተከሰተ ግጭት መጠለያ ውስጥ የነበሩ ቢያንስ ስድስት ተፈናቃዮች መገደላቸውን ባደረገው ማጣራት ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡ ሁለቱ ክልሎች በቅንጅት በመሥራት በአካባቢው ለተከሰተው ግጭት ምክንያት ለሆኑ ጉዳዮች ሰላማዊ መፍትሔ በመስጠት፣ የነዋሪዎችንና የተፈናቃዮችን ደኅንነት በዘላቂነት የማረጋገጥ ሥራ እንዲያከናውኑ፣ ለደረሰው ጉዳት ተጎጂዎች እንዲካሱና ተገቢ የሆነ ጥንቃቄ ባለማድረግ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጉዳት እንዲደርስ ባደረጉ የፀጥታ ኃይሎች አባላት ላይ አስፈላጊው ምርመራ ተደርጎ ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያስፈልጋል ብሏል፡፡ በካምፓላ ስምምነት መሠረት የመንግሥት የፀጥታ አካላት የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች የሚገኙባቸውን የመጠለያ ጣቢያዎች ደኅንነት አደጋ ላይ ሊጥሉ ከሚችሉ ድርጊቶች መቆጠብ እንዳለባቸው አስገንዝቧል፡፡ ይህንንና ሌሎች መሰል አሳሳቢ ችግሮችን ከግምት በማስገባት፣ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ የሚስተዋሉ ግጭቶች በሙሉ ሁሉን አሳታፊ መፍትሔ ይፈለግላቸው!