Monday, December 11, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊበሽታዎችን በዘረመል ደረጃ ለመመርመር የላቦራቶሪውን አቅም የሚያዘምነው ፕሮጀክት

በሽታዎችን በዘረመል ደረጃ ለመመርመር የላቦራቶሪውን አቅም የሚያዘምነው ፕሮጀክት

ቀን:

በ21ኛው ምዕት ዓመት ወረርሽኞች (ዚካ፣ ዴንጊ፣ ኢቦላ፣ ሳርስን) የጨመሩ ሲሆን፣ የቅርብ ጊዜው አስከፊው ወረርሽኝ ኮቪድ-19 ነው። ባለፉት ጥቂት አሠርታት ውስጥ በርካታ ተላላፊ በሽታዎች መከሰታቸውን ተከትሎ፣ ለሕዝብ ጤና አጠባበቅ በተገቢው ጊዜ በሽታ አምጪ ስለሆኑት ነገሮች መረጃ/ዳታ ማሰባሰብ ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ አስፈላጊ ሆኗል።

የበሽታዎች ቅኝትን ዘመናዊ የሚያደርግ፣ ሳይንቲስቶች ምርምር የሚያደርጉበት፣ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ የትምህርት ዕድል የሚያገኙበትና ጥናትና ምርምር የሚያደርጉበት፣ የመመርመሪያ መሣሪያዎችም በአገር ውስጥ የማምረት አቅምን የሚጨምር ‹‹ኢፒጂ ኢትዮጵያ›› (EpiGen)  የተሰኘ ፕሮጀክት መስከረም 7 ቀን 2016 ዓ.ም. ይፋ ተደርጓል፡፡

በጤና ሚኒስቴር አስተባባሪነት የአውሮፓ ኅብረት፣ ከኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር በመሆን የሚከናወነው የኢፒጂን ፕሮጀክት፣ የተለያዩ በሽታዎች ምንነትና በሽታዎች በቆይታቸው የሚያመጡትን ለውጥ በ‹ጂኖሚክ ሲኩዌንስ› በሚባል ቴክኖሎጂ ማለትም በተህዋስያኑ በዘረመል ደረጃ ለመለየትና ለመመርመር የሚያስችል ፕሮጀክት ነው፡፡

ፕሮጀክቱ  ለጤና ሚኒስቴር፣ በጤና ዙርያ ለሚሠሩ ባለድርሻ አካላት ጉዳዩን ለማሳወቅና ፕሮግራም ለመቅረፅ፣ ለፖሊሲ ዝግጅት ግብዓት ለማድረግ ታስቦ መቀረፁን የገለጹት የጤና ሚኒስትር አማካሪ መብራቱ መሰቦ (ዶ/ር)፣  ሳይንቲስቶቹ የአገር ውስጥ አቅምን ከፍ ለማድረግ የሚረዱ ጥናቶች ላይ በትኩረት እንዲሠሩ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

የጤና ሚኒስትር አማካሪው፣ በሽታዎች አሉ የሉም ብሎ በአገር ውስጥ አቅም አስቀድሞ ለመረዳትና ለማሳወቅ የሚያስችል ሙሉ አቅም እንደ አገር እንዳልነበር ጠቁመው፣ በተለይ ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ ጋር ተያይዞ ባለፉት ሦስት ዓመታት ከፍ ያለ የአገር ውስጥ አቅም ለመፍጠር፣ በላቦራቶሪ፣ በሰው ኃይል፣ የበሽታዎችን ቅኝትን ከፍ ከማድረግ አንፃር ጤና ሚኒስቴር በርካታ ሥራዎች ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰዋል።

ፕሮጀክቱን በይፋ ያስጀመሩት የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ቶሌራ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ፕሮጀክቱ ተላላፊ በሽታዎችን ለመቆጣጠር ያስችላል፣ የምርምር አቅምን ያጠናክራል፡፡

አምስት ዓመት የሚቆየው ፕሮጀክቱ ከመላው ኢትዮጵያ በተመረጡ ሆስፒታሎች የሚተገበርና ከሦስት መቶ ሆስፒታሎች መረጃ በመሰብሰብ ችግሮችን በመለየትና መፍትሔ በማስቀመጥ አቅጣጫ የሚሰጥበት፣ የየጤና ተቋማት ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና እንዲያገኙ የሚደረግበት መሆኑንም አስታውቀዋል።

ፕሮጀክቱ በአውሮፓ ኅብረት ፈንድ የሚደረግ ሆኖ፣ የአውሮፓ አባል አገሮች የሆኑት የጀርመን፣ የስፔን እና የኔዘርላንድ ዩኒቨርሲዎች፣ ከአገር ውስጥ ደግሞ የአርማወር ሃንሰን ሪሰርች ኢንስትቲዩትና አምስት ዩኒቨርስቲዎች የተካተቱበት ፕሮጀክት መሆኑንም ገልጸዋል።

የማክማስተር ዩኒቨርስቲ ተመራማሪ የሆኑ ዳዊት ወልዳይ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የኢፒጂ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት ኢትዮጵያውያን ሳይንቲስቶች አውሮፓ ካሉ አጋር የጥናት ኢንስትቲዩት ጋር በመተባበር ፕሮጀክት ቀርፆ በማቅረብና አሸናፊ በመሆን ወደ አገር ማምጣት መቻሉን ተናግረዋል።

ፕሮጀክቱ የሚያጠነጥነው ተላላፊ በሽታዎች ገና ከመከሰታቸው በፊት፣ ወይም በሽታው በተከሰተ ከ24 ሰዓት በፊት በዘረመል በመመራመር፣ መረጃን በአፋጣኝ ለውሳኔ ሰጪ ማለትም ለጤና ሚኒስቴር ለማስተላለፍ እንዲቻልና አቅምን ለመገንባት መሆኑንም አስገንዝበዋል፡፡

ከአምስተርዳም ኢንስቲትዩት ፎር ግሎባል ሄልዝ ዴቨሎፕመንት (AIGHD) የመጡት ቶብያስ ሪንክ ዲዊት (ፕሮፌሰር)፣ የኢፒጂን ኢትዮጵያ አጠቃላይ ሁኔታን አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ በገለጻቸው፣ በአየር ንብረትና በሌሎች ምክንያቶች ሳቢያ በሽታዎችና ወረርሽኞች የመከሰት ሁኔታ መበራከቱን፣ ለዚህም አስቀድሞ መዘጋጀቱ ላይ በትኩረት ሊሠራ ይገባል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ የበሽታ ምርመራን ማሻሻል በምርመራ ሒደት ያሉትን ክፍተቶች ለመሙላት በጋራ እንደሚሠራም ቃል ገብተዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ለሰው ልጅ መብት መከበር ስናወራ 75 ዓመት ሞላን!

በገነት ዓለሙ ዓለም ስለሰብዓዊ መብቶች ሲያወራ፣ ሲምል፣ ሲገዘት፣ ሲፈጠም፣ ቃል...

ካልተማከለ የካፒታል ገበያ ወደ ዘመናዊና የተደራጀ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ

በእሱፈቃድ ተረፈ በአገራችን የካፒታል ገበያ አዋጅ መውጣትን ተከትሎ የተማከለ የሰነደ...

ለማይቀረው ምክክርና ድርድር እንዘጋጅ

በያሲን ባህሩ  የዘመናዊት ኢትዮጵያ ፖለቲካ ውዝግብ በትንሹ የአንድ ምዕተ ዓመት...

ደንብ አስከባሪዎች ደንብ ያክብሩ!

በአዲስ አበባ ከተማ ደንብ አስከባሪዎች፣ ሌሎች የፀጥታ አካላት፣ እንዲሁም...