የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 78ኛው ጠቅላላ ጉባዔ በኒውዮርክ ከተማ በመካሄድ ላይ ሲሆን፣ ከ140 በላይ የዓለም መሪዎችና ተወካዮች በመሰብሰብ አንገብጋቢ በሆኑ የዓለም ጉዳዮች ላይ እየተወያዩ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ በጣም ከሚጠበቁት ዓመታዊ ኩነቶች አንዱ በሆነው ጉባዔ፣ መሪዎችን በተመለከተ ለ15 ደቂቃ በሚያደርጉት ንግግሮች የዓለም አቀፍ ጉዳዮችን ለመፍታት መድረክ ይሰጣቸዋል።
በፀጥታው ምክር ቤት ከአምስቱ ቋሚ አባላት መካከል በፕሬዚዳንቱ ጆ ባይደን የምትወከለዋ አሜሪካ ናት። የዩክሬን ፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ፣ ሩሲያ በአገራቸው ላይ በየካቲት 2022 ሙሉ ወረራ ከፈጸመች በኋላ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በአካል በጠቅላላ ጉባዔው ላይ ተገኝተው ንግግር እንደሚያደርጉ ይጠበቃል፡፡

በተለያዩ ሚዲያዎች እንደተዘገበው፣ በጉባዔው በአጀንዳነት ከተያዙት መካከል የአየር ንብረት ቀውስና የዩክሬን ጦርነት ይገኙበታል፡፡ ከ140 በላይ መሪዎችና የአገሮች ተወካዮች የዓለም መሪዎችና የአገር መሪዎች ለቀጣዩ ዓመት (2024) ቅድሚያ የሚሰጧቸውን ነገሮች እንዲለዩ ዕድል ከመስጠቱም በላይ በፈታኝ ጉዳዮች ላይ ኅብረት እንዲፈጥሩ ያስችላቸዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ ባለፈው ሳምንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ‹‹ከየዓለም ማዕዘናት የመጡ መሪዎች የዓለምን ሁኔታ መገምገም ብቻ ሳይሆን፣ ለጋራ ጥቅም መሥራታቸው በየዓመቱ የሚጠበቅ ቢሆንም፣ ‹‹ዓለም አሁን የሚፈልገው ተግባር ብቻ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የዘንድሮው ጉባዔ መሪ ቃል ‹‹መተማመንን መልሶ ማቋቋምና ዓለም አቀፋዊ ትብብርን ዳግም ማደስ፣ አጀንዳ 2030 እና የዘላቂ ልማት ግቦች ትግበራን በማፋጠን ሰላም፣ ብልፅግና፣ ዕድገትና ዘላቂነት ለሁሉም መፍጠር›› የሚል ነው።
ከዝግጅቱ ጎን ለጎን ተከታታይ የሁለትዮሽ ውይይቶችም እንደሚያካሂድ ይጠበቃል፡፡
ከሚገኙት መሪዎች መካከል የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ አንዱ ናቸው፡፡ በጠቅላላ ጉባዔው ንግግር እንደሚያደርጉና ጎን ለጎን ከባይደን ጋር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል።
የዓምናው ጉባዔ ከተመለከታቸው መሪ ሐሳቦች መካከል ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ ለማገገም የሚደረጉ ጥረቶችን፣ የሩሲያ ዩክሬንን መውረርና የአየር ንብረት ለውጥ ዘንድሮም በጉልህ ይታያሉ ተብሎ ይጠበቃል።
በመንግሥታቱ ድርጅት የአሜሪካው ተወካይ ቶማስ ግሪንፊልድ፣ በኦገስት መገባደጃ ላይ ለጋዜጠኞች ሲናገሩ፣ አብዛኞቹ የምዕራባውያን አገሮች ሩሲያ ወታደሮቿን ከጎረቤት ዩክሬን እንድታስወጣ ከፍተኛ ጫና እንዲያደርጉ ትጠብቃለች።
የዘላቂ ልማት ግቦችን በተመለከተ የአገሮች መሪዎች የሚሳተፉበት ጉባዔ የሚካሄድ ሲሆን፣ የልማት ግቦቹን የእስካሁን አፈጻጸምና ቀጣይ ትግበራ ላይ እንደሚመክር ተገልጿል።
ከሚመከርባቸው አጀንዳዎች መካከል መሠረታዊ የጤና አገልግሎት ሽፋንን፣ የአየር ንብረት ለውጥን፣ የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ አደጋዎችን ስለ መከላከልና አፋጣኝ ምላሽ ስለመስጠት ይጠቀሳሉ።
በዚሁ ጉባዔ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ባለሥልጣንን ያቀፈ ልዑክ የሚገኝ ሲሆን፣ በ55 አጀንዳዎች ላይ ንግግር በማድረግ የኢትዮጵያን አቋም ይፋ እንደሚያደርግ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ መለስ ዓለም (አምባሳደር) መሰንበቻውን ለሚዲያ በሰጡት መግለጫ መናገራቸው ይታወሳል፡፡
በ78ኛው የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባዔ ኢትዮጵያ የነቃ ተሳትፎ ለማድረግ ዝግጅት ማድረጓን መግለጻቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያ መድረኩን በመጠቀም ብሔራዊ ጥቅሞቿ እንዲረጋገጡና አኅጉራዊ አጀንዳዎች እንዲሳኩ ለማድረግ በቂ ዝግጅት ማድረጓንም መናገራቸው ይታወሳል፡፡