በአንድ መንደር ውስጥ አግብታ ብዙም ሳትቆይ ባሏን በሞት የተነጠቀች አንዲት ሴት ትኖር ነበር፡፡ አጠገቧ ዓይኗን የምታሳርፍባትና የምታጽናናት ብቸኛ ልጅ ነበረቻት፡፡ አንድ ልጇንም በርኅራኄና በፍቅር አሳደገቻት፡፡ ይሁን እንጂ በጥንቃቄ ብታሳድጋትም ልጇ ካደገች በኋላ የበለጠ ወደ ዓለም አዘነበለችና መንደሯን ለቅቃ ወደ ዋናው ከተማ ጥላት ኮበለለች፡፡ የልጅቷ እናት በሐዘን ተሰብራ ልጄ ከዛሬ ነገ ትመለስ ይሆናል ብላ ብትጠብቃትም እሷን የበላው ጅብ አልጮህ አለ፡፡
የኮበለለችው ልጇ እንድትመለስ ሌትና ቀን እየጸለየች ዓመታት አለፉ፡፡ አንድ ምሽት አንድ የእግር ዱካ ድምፅ ወደ ቤቷ በሚወስደው ጠባብ መተላለፊያ እየተቃረበ ሲመጣና ወደ በሩም ተጠግቶ የበሩን እጀታ እየፈራ እየተባ ሲነካ ሰማች፣ እጀታውም ድምፅ አሰማ፡፡ በእንቅልፍ ሰመመን እንዳለች አንድ ሰው ወደ ውስጥ መዝለቁን እናት ትሰማና ካልጋዋ ተፈናጥራ በመነሳት ወደ በሩ ታመራለች፡፡ የኮበለለችው ልጇ ናት፡፡ ልቧ በደስታ እየዘለለ ልጇን በፍቅር በእቅፏ ውስጥ ወሸቀቻት፡፡ እንደተቃቀፉም፣ ልጇ፣ ‹‹እማዬ፣ በዚህ በእኩለ ሌሊት ለምን በሩን አልቆለፍሺውም?›› ብትላት፣ እናት የልጇን ጸጉር እየደባበሰች፣
‹‹ልጄ ሆይ፣ አንቺ ከኮበለልሽበት ቀን ጀምሮ ምናልባት አንድ ቀን ስትመለሺ ልትቀበልሽ ሁሌ ዝግጁ የሆነች እናት እንዳለሽ እንድታውቂና ሳታመነቺ እንድትገቢ በማሰብ በሩ በቀንም ሆነ በሌሊት ተቆልፎ አያውቅም›› ስትል መለሰችላት፡፡
- ኃይሌ ከበደ ‹‹ምስካይ›› (2004)
******