የግል የጤና ዘርፍ የሚሰጡ የሕክምና አገልግሎቶች ለኅብረተሰቡ በፋይናንስ ተደራሽ እንዲሆኑ የአሠራር፣ የፖሊሲና የሕግ ማሻሻያ የማድረግ፣ የክትትና የድጋፍ ሥርዓት መዘርጋት እንደሚገባ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ኮሚሽኑ ይህንን ያለው ሰኔ 2014 ዓ.ም. እስከ ሰኔ ወር 2015 ዓ.ም. በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱ ሁነቶች ሳቢያ የተስተዋሉትን አጠቃላይ የማኅበራዊና የኢኮኖሚያዊ መብቶችን ሁኔታ የሚዳስሰው ሪፖርቱ ላይ ነው፡፡
በቂ የሆነ የኑሮ ደረጃ የመኖር መብት፣ ትምህርት የማግኘት መብት፣ ሊደርስ የሚችል ከፍተኛ አካላዊና አዕምሯዊ ጤና የማግኘትና የሥራና ተያያዥ መብቶችን በኢትዮጵያ ዋና ዋና አሳሳቢ ጉዳዮች ብሎ በዝርዝር አስቀምጧል፡፡
የግሉ የጤና ዘርፍ በጤና ተደራሽነት ያለው ሚና ከፍተኛ ቢሆንም፣ በመድኃኒት፣ በሕክምና ግብዓቶች አቅርቦት ዝቅተኛ መሆን፣ በመንግሥት በኩል የሚደረገው ድጋፍ አናሳ መሆን፣ በቁጥጥርና ክትትል ማነስ ምክንያት ለኅብረተሰቡ ከፋይናንስ አንፃር ተደራሽ አለመሆኑን ኢሰማኮ ባደረገው ክትትል ሥራ መረዳቱን ገልጿል፡፡
ኮሚሽኑ በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣው የፀጥታ ችግር፣ ከፍተኛ ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳቶችና በዚህም ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውስ ማስከተሉን በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች ከሚያዝያ ወር 2015 ዓ.ም. ጀምሮ በተከሰተው ግጭትና አለመረጋጋት በሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት ከማድረሱ በላይ፣ ወቅቱ የግብርና ሥራ ቅድመ ዝግጅት የሚደረግበት በመሆኑ፣ አርሶ አደሩ ተረጋግቶ መሥራት እንዳልቻለና ይህም ዜጎች ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመረጋጋት እንደፈጠረባቸው ጠቅሷል፡፡
ግጭቱ በክልሉ አሁንም የቀጠለና ዕልባት ያልተበጀለት በመሆኑ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውሱ ተባብሶ መቀጠሉ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በተደጋጋሚ በሚፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት የዝርፊያዎች፣ የመፈናቀሎች፣ የቤተ እምነቶች መቃጠል ኅብረተሰቡ ተረጋግቶ የዕለት ተዕለት ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ሕይወቱን እንዳይመራ ማድረጉ ተገልጿል፡፡
ይህም በርካታ ነዋሪዎች ያለ መጠለያ እንዲኖሩ፣ የሕክምና አገልግሎት እንዳያገኙና በሺዎች የሚቆጠሩ ሕፃናት ከትምህርት ገበታቸው ውጪ እንዲሆኑ ምክንያት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች የአፈር ማዳበሪያ ለገበሬው ወቅቱን ጠብቆ ባለመቅረቡ የግብርና ሥራ መስተጓጎሉን የጠቀሰው ሪፖርቱ፣ በዚህ ምክንያት በተለያዩ አካባቢዎች ያለው የፀጥታ ችግርና የትጥቅ ግጭት፣ በተለይም በምግብ ምርት አቅርቦትና ዋጋ ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ መፍጠሩን ገልጿል፡፡
በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የተከሰተው ድርቅ ከፍተኛ መሆኑን የጠቀሰው ሪፖርቱ፣ በመንግሥት በኩል ለዚህ ችግር የቅድመ መከላከል ሥራ በበቂ ሁኔታ አለመሠራቱ ችግሩን የከፋ እንዲሆን ማድረጉ ተዘርዝሯል፡፡
በተለይ በአማራ፣ በአፋርና በትግራይ ክልሎች በሰሜኑ ጦርነት ሳቢያ ቁጥራቸው ከፍ ያሉ ትምህርት ቤቶችና የትምህርት ቁሳቁሶች መውደማቸውንና መዘረፋቸው በሪፖርቱ ተጠቅሶ፣ የተጎዱ ክልሎች መልሶ ለመገንባት የሚደረገው ጥረት በቂ ካለመሆኑም በላይ፣ ግጭቶች በቀጠሉባቸው አካባቢዎች ችግሩን ይበልጥ ውስብስብ አድርጎታል፡፡
በሰሜኑ ጦርነት ምክንያት በአፋር፣ በአማራና በትግራይ ክልሎች በጤና ተቋማት ላይ የደረሰው ውድመትና ዝርፊያ በጤና መብት ተደራሽ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡
በተለይም የእናቶችና የሕፃናት ጤና ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳደረ መሆኑ፣ በዚህም ሳቢያ የእናትቶችና የሕፃናት ሞት ቁጥር መጨመሩን ተገልጿል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ‹‹ፀጥታና ደኅንነት ሥጋት›› በሚል የንግድና የመኖሪያ ቤቶች መፍረሳቸውን፣ በማፍረስ ሒደቱ ልዩ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው አካል ጉዳተኞች ጭምር ተጎጂ ስለመሆናቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡
ተጎጂዎች ቅሬታቸውን ለማቅረብ በሄዱባቸው ቦታዎች ማዋከብና እንግልት እንደደረሰባቸው፣ ምንም እንኳን ፈረሳው ለጊዜው የቆመ ቢሆንም፣ አሁንም ተገቢውን ፍትሕ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
ሪፖርቱ የኢኮኖሚያዊ፣ የማኅበራዊና የባህል መብቶች የሕግ ማዕከሉን ያማከለ መሆኑን፣ ዓለም አቀፍ መብቶችን፣ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ዓለም አቀፉ ቃል ኪዳንና ሌሎችንም መብቶች ያማከለ ሪፖርት ነው፡፡