አዲሱ የኢትዮጵያ ዓመት 2016 ሊገባ ሁለት ቀን ይቀረዋል። ዛሬ እሑድ ጳጉሜን 5 ቀን እንዳለፉት ሦስት ዓመታት ቢሆን ኖሮ፣ ዓመቱ 365ኛ ቀን ላይ ያበቃ ነበር። ነገር ግን ከየዓመቱ የተሰበሰበችው ሩቧ 6 ሰዓት 2015ን ወደ 366 ቀኖች ኣሳድጋለች። ሠግር/ ሳጋ የምትባለዋን ጳጉሜን 6ኛ ቀንን አስገኝታለች።
ማክሰኞ መስከረም 1 ቀን “ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ” ለማለት ሕዝበ ኢትዮጵያ እየተዘጋጀ ቢሆንም በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተፈጠሩት ግጭቶችና ያለመረጋጋቶች፣ ተከትለው የመጡት ሞቶችና ጉዳቶች፣ መፈናቀሎችም በርዕሰ ዓውደ ዓመቱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ፈጥረዋል። ሐዘንና ልቅሶንም(ብካይንም) አስከትለዋል። ሆኖም የሕይወት ዑደት ቀጥሏል።
መስከረም ሲጠባ
ደራሲው በዓሉ ግርማ “ደራሲው” በተሰኘውና በ1972 ዓ.ም. ባሳተመውየልቦለድ ድርሰቱ ዕንቁጣጣሽን እንዲህ ነበር የገለጻት። እንጥቀስ።
‹‹መስከረም ጠባ፡፡ የመስከረም ጮራ ዕንቁጣጣሽ ብላ ተግ አለች፡፡
ልጃገረዶች ሳዱላቸውን አሳመሩ፡፡ አደስ ተቀቡ፡፡ እንሶስላ ሞቁ፡፡ ወንዝ ወረዱ፡፡ ቄጤማ ለቀሙ፡፡ ፀአዳ ልብሳቸውን ለብሰው፣ አሽንክታባቸውን አጥልቀው፣ ‹አበባዬ ሆይ – ለምለም› በማለት ተሰብስበው ብቅ አሉ – እንደ ጮራይቱ፡፡ የወርሀ መስከረም ብሩህ ተስፋና ስሜት በምድሪቱ አስተጋባ፡፡ ጠፍ እያለ መጣ ምድሩ፡፡ ወንዙም እየጠራ፡፡ ኩል መሰለ ሰማዩ፡፡ ሜዳው፣ ጋራው፣ ሸንተረሩ ወርቃማ የአደይ አበባ ካባ ለበሰ፡፡ ደመራ ተደመረ፡፡ ተቀጣጠለ ችቦ፡፡ ‹ኢዮሃ አበባዬ – መስከረም ጠባዬ› ተባለ፡፡››
ይህ ሥዕላዊና የመስከረም ድባብ የተገለፀበት ሐተታ አዲሱ ዓመት በመጣ ቁጥር ባነበቡት ዘንድ የሚታወስ ነው፡፡
ይህም ሆኖ ‹‹ኢዮሃ አበባዬ . . . መስከረም ጠባዬ›› ዘመን በተሞሸረ ዓመት በተቀመረ ቁጥር ሰው መልካም ምኞት የሚለዋወጥበት ሐረግ ነው፡፡ ድምፃውያንም ያቀነቅኑታል፡፡ እንግዲህ ኃያሉ ክረምት ሊያበቃ፣ መሰስ እያለ ወጥቶ ለከርሞ ሊመለስ የሚጠብቀው መስከረም 25 ቀን 2016ን ነው፡፡
ግን ኢዮሃ እየተባለ የመዘመሩ፣ የማቀንቀኑ ምስጢር ምንድን ነው? ኢዮሃስ ምን ማለት ነው? ሊቁ አለቃ ደስታ ተክለወልድ ዘብሔረ ወግዳ፣ በታላቁ ‹‹አዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት›› ሥራቸው ያወሱትን እዚህ ላይ ይወሳል፡፡ ሥርወ ቃሉ (የቃሉ ሥር መገኛ) ‹‹ኢዩ››- እይ፣ ‹‹ሃ››- ውሃ ማለት ሲሆን፣ ሲናበብ ደግሞ ‹‹ውሃ ያደረገውን እይ ተመልከት›› የሚል ፍች ይኖረዋል፡፡ ኢዮሃ አበባዬ የደስታ ቃል ነው፡፡ ወንዶች የደመራ ለት እየዘፈኑ ድምሩን የሚዞሩበት ያበባ ዘፈን ነው፡፡ ሰኔ ግም ብሎ፣ ያምሌን ጨለማ አልፎ፣ የነሐሴን ጎርፍ ሙላትን በእኝኝ ተሻግሮና ተንተርሶ በጠንካራው ዝናብ (ውሃ) ምክንያት ብቅ የምትለዋ ያደይ አበባ ናትና፤ ውሃ ያደረገውን ታምር፣ ያስበቀለውን አበባ አደያዊን ተመልከት ለማለት ‹‹ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ›› ይባላል፡፡
‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ ጥያቄዎችና ባሕሎች›› በሚሉት መጽሐፋቸው ሀብተማርያም አሰፋ (ዶ/ር) መስከረምን እንዲህ ገልጸዋታል፡፡
መስከረም ‹‹ምስ-ከረም›› ከከረመ በኋላ ወይም ክረምት ካለፈ በኋላ ማለት ነው፡፡ የመስከረም ወር ዝናብ የሚቆምበት ፀሐይ የምትወጣበት ወንዞች ንጹሕ ውሃ ጽሩይ ማይ የሚጎርፍበት፣ አፍላጋት የሚመነጩበት፣ አዝርዕት ማለት የተዘሩት አድገው ማሸት የሚጀምሩበት፣ ሜዳዎችና ተራራዎች ሸለቆዎችም በአበባ የሚያሸበርቁበትና የሚቆጠቆጡበት ነው ይሉታል፡፡
እንዲህም በመሆኑ የጨለማ የችግርና የአፀባ ጊዜ የሚያበቃበት የብርሃን፣ የደስታ የሸት፣ የፍሬና የጥጋብ ጊዜ የሚጀምርበትና የሚተካበት ነው ብሎ ሕዝቡ ስለሚያምንበትም የዕንቁጣጣሽ በዓልን ከሁሉ አብልጦ ግምት ስለሚሰጠው በእሳት ብርሃንና በእሳት ቡራኬ በየቤቱ እንደ ሁኔታው እንስሳ አርዶ ደም አፍስሶ ይቀበለዋል፡፡ ያከብረዋል ሲሉም አክለውበታል፡፡
በወርኃ መስከረም መሬቷ በአደይ አበባ አሸብርቃ ስለምትታይና በተለይም ዕንቁ የመሰለ አበባ ስለምታወጣ መሬቷን ዕንቁጣጣሽ፣ ዕንቁ የመሰለ አበባ አስገኘሽ ለማለት ዕንቁጣጣሽ መባሏን የባህል ባለሙያው መምህር ዓለሙ ኃይሌ ይገልጻሉ፡፡ አያይዘው አቧራ፣ ቡላ የነበረው መሬት በዝናቡ ኃይል ለምልሞ ተመልከቱኝ፣ ተመልከቱኝ የምትል ያሸበረቀች፣ አበባ የተንቆጠቆጠች ሆነች የሚል ለዕንቁጣጣሽ ስያሜ መነሻ ሊሆን እንደሚችል ይጠቁማሉ፡፡
እንግጫ
እንግጫ የሣር ዓይነት ነው፡፡ በአዲስ ዓመት ዋዜማ ልጃገረዶች መስክ ወርደው የሚነቅሉት ነው፡፡ የዕንቁጣጣሽ ብሥራት ነጋሪ ነው፡፡ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ባሳተመው ‹‹በሰሜን ሸዋ በምሥራቅና ምዕራብ ጎጃም ዞኖች የተመዘገቡ የኢንታጀብል ባህላዊ ቅርሶች›› መድበል ላይ ስለ እንግጫ እንደሚከተለው ተገልጿል፡፡
በዘመን መለወጫ ዋዜማ እንግጫ ሳር በልጆች እየተነቀለ እንደቋጨራ እየተጎነጎነ ጣራ ላይ ተወርውሮ ያድርና ጠዋት ላይ ለዘመን መለወጫ እየተጎነጎነ ራስ ላይ፣ ቡሃቃ አንገት ላይና ሌማት ክዳን ላይ ይታሰራል፡፡ ቡሃቃ እና ሌማት ላይ የመታሰሩ ምልክትነት ለረድኤትና ለበረከት ሲባል የሚደረግ ነው፡፡
ራስ ላይ የታሰረው ደግሞ ለመስቀል በዓል ተቀምጦ ይቆይና ደመራው ላይ ይታሰርና እንዲቃጠል ይደረጋል፡፡ ለራስ ምታትና ለጤንነት ሲባል በማኅበረሰቡ የሚከወን ነው፡፡
እንግጫ ነቀላ ዘመን ሲለወጥ የሚከወን ባህላዊ ሥራት ነው፡፡ በዋዜማው ያላገቡ ሴቶች ወደ መስክ ወርደው እንግጫ ይቆርጣሉ፡፡ ምሽቱን ደግሞ እንግጫውን ሲጎነጉኑ ይቆያሉ፡፡ ሲነጋ ደግሞ በጠዋት ተጠራርተው በመሰባሰብ በየሰው ቤት እየዞሩ የተጎነጎነው እንግጫ ከቤቱ ምሰሶ ላይ ያስራሉ፡፡ እንግጫ የአዲስ ዓመት የምሥራች ምልክት ነው፡፡ በመድበሉ እንደተወሳው፣ እንግጫው ነቀላ በዜማ የታጀበ ነው፡፡
‹‹እቴ አበባዬ ነሽ
አደይ ተክለሻል
አደይ ተቀምጠሻል
ባሶና ሊበን
አዋጋው ብለሻል
ቦሶና ሊበን
ምነው ማዋጋትሽ
አንዱ አይበቃም ወይ››
በዚህ ጊዜ ወንዶች ደግሞ ያዘጋጁትን ዳቦት (የችቦ ስም) በእሳት ለኩሰው እያበሩ በመምጣት እንግጫ ለሚጎነጉኑት ሴቶች ያበሩላቸዋል፡፡ ዳቦታቸውን እያበሩ ወደ ሴቶቹ በሚያመሩበት ጊዜ የሚያዜሙት ዜማ አላቸው፡፡
‹‹ኢዮሃ ኢዮሃ
የቅዱስ ዮሐንስ
የመስቀል የመስቀል
አሰፉልኝ ሱሪ
ኢዮሃ›› በማለት ያዜማሉ፡፡
በከተሞች አካባቢ እንግጫ ነቀላው እየቀረ አበባዮሽ የሚለው ጨዋታ በመስፋፋት ላይ ይገኛል፡፡ ልጃገረዶቹ ወደየሰው ቤት ሲሄዱ ሎሚ ይሰጣቸው የነበረ ሲሆን፣ አሁን ላይ ግን የእንግጫው ሴቶች ራሳቸው ‹‹እንኳን አደረሳችሁ›› እያሉ ሎሚ ሲሰጡ ገንዘብ ይሰጣቸዋል፡፡
የዘመን አዋጅ
መስከረም አንድ ቀን ያለው ልዩ ነገር የዘመኑን መለወጥ አስመልክቶ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የባሕረ ሐሳብ አዋጁ ይነገራል፡፡ በዓመቱ ውስጥ በዓል የሚውልበት፣ ጾም የሚገባባትን ቀን መምህራኑ እያሰሉ ይናገሩታል፡፡ ዓመቱን በፀሐይና በጨረቃ፣ በዓመተ ዓለም ይገልጹታል፡፡ ዘመኑን ያውጃል፣ የባሕረ ሐሳቡን ጥንተ ታሪክ ይናገራል፡፡ አዲሱ ዓመት 2016 ዓ.ም. ከአዲስነቱ ባሻገር የአራት ዓመት ዓውድ ማብቂያም ነው፡፡
2016 በተለያዩ አቆጣጠሮች
ቀጣዩ 2016 በፀሐይ አቆጣጠር፣ የዓለም ፍጥረት መነሻ በሆነው በዓመተ ዓለም ሲቆጠር 7516 ዓመተ ዓለም መሆኑና ስምንተኛው ሺሕ ከገባ 516ኛ ዓመት ላይ መገኘቱን ስሌቱ ያሳያል፡፡
በኢትዮጵያ የፀሐይና ጨረቃ ጥምር አቆጣጠር መሠረትም 2024 ዓ.ም. መስከረም 1 ቀን ላይ ይገባል፡፡
መስከረም 1 በኢትዮጵያ የጨረቃ አቆጣጠር መሠረት መስከረም 26 ቀን 2024 በኢትዮጵያ እስልምና ትውፊትም ዕለቱ ሠፈር 26 ቀን 1445 ዓመተ ሒጅራ፣ እንደ ኢትዮጵያ አይሁድ (ቤተ እስራኤል) ትውፊትም ኢሉል 26 ቀን 5783 ዓመተ ፍጥረት አዲሱን ዓመት ኢትዮጵያውያን ይቀበሉታል፡፡
የመስከረም ወቅት
መስከረም 1 በክረምት ውስጥ የምትገኝ ያመት መነሻ ናት፡፡ ሰኔ 26 ቀን የገባው ክረምት የሚወጣው መስከረም 25 ቀን ላይ ነው፡፡ የስድስተኛው ምዕት ዓመት የነገረ መለኮት ሊቁ (ቲኦሎጊያን)፣ መዝሙረኛውና ዜማ ቀማሪው ቅዱስ ያሬድ በመጽሐፈ ድጓው ‹‹ኀለፈ ክረምቱ ጸገዩ ጽጌያት ቆመ በረከት!›› – ክረምቱ አለፈ አበቦችም ፈኩ፣ በረከትም ቆመ ይለናል፡፡
የዛሬው ቀን ጳጉሜን 5 ቀን 2015ም ሆነ መስከረም 1 ቀን 2016 ዓ.ም. በክረምት ውስጥ ይገኛሉ፡፡ እንደ ቅዱስ ያሬድ አመዳደብ፣ በውስጡም ልዩ ልዩ ንኡሳን ክፍሎች አሉት፡፡ ከነሱም መካከል የነሐሴ መጨረሻና የጳጉሜን ሳምንት ‹‹ጎሕ፣ ጽባሕ››- ወጋገን፣ ንጋት ይለዋል፡፡ ይህም ያዲስ ዘመን መስከረም የሚጠባበት ጊዜ መድረሱን አመላካች ነው፡፡
ሌላው ንኡስ ክፍል ከዓመት አውራ መነሻ (ርእሰ ዐውደ ዓመት) መስከረም 1 ቀን እስከ መስከረም 7 (8) ቀን ያለው ‹‹ዮሐንስ›› ሲባል፣ ከመስከረም 9 እስከ 15 ዘመነ ፍሬ ይባላል፡፡ ‹‹ዮሐንስ›› የሚለው ቃል የተወሰደው በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ከሚገኘውና እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስን ካጠመቀው የዘካርያስ ልጅ ዮሐንስ ነው፡፡ መስከረም 1 ቀን ቅዱስ ዮሐንስ፣ ዕለተ ዮሐንስ መባሉ በተምሳሌታዊ ፍች የመጣ ነው፡፡ ከአሮጌው ብሉይ ኪዳን ወደ ሐዲስ ኪዳን፣ ወደ ዓመተ ምሕረት መሸጋገሪያ ላይ የመጣው መንገድ ጠራጊው ዮሐንስ ስለሆነ፤ ባህሉ/ ትውፊቱ ካሮጌው ዓመት ወዳዲሱ መሸጋገሪያዋን ዕለት፣ መስከረም 1 ቀንን በዘይቤ ‹‹ቅዱስ ዮሐንስ›› ‹‹ዕለተ ዮሐንስ›› እያለ ይጠራዋል፡፡ ከጥንት እስከ ዛሬ ባገልግሎት ላይ ይገኛል፡፡
ሊቁ እጓለ ገብረ ዮሐንስ (ዶ/ር)፣ የዛሬ 54 ዓመት በአዲስ አበባ ራዲዮ ጣቢያ የዘመን መለወጫ በዓል ዋዜማ ላይ፣ ባደረጉት ንግግር ማሰሪያቸውን እንዲህ ገልጸውት ነበር፡፡ እኛም እንጋራዋለን፡፡
‹‹በዘመን መለወጫ በዓል አሮጌው አልፎ አዲስ ሲተካ የክረምት ጭለማ አልፎ ብርሃን ሲመጣ ሁሉም ‹በተውሳከ መብልዕ ወመስቴ› [ምግብና መጠጥን በመጨመር] እየተደሰተ፣ ከአንዱ ዘመን ወደ ሌላው መሻገሩን በሚያከብርበት ዕለት ትንሽ ጊዜ አስተርፎ ስለጠቅላላው የሕይወት ጉዞ ለሚያስበው ረድኤት ይሆን ዘንድ፣ ለማያስበው ደግሞ እንዲያስብ ምክንያት ይሆን ዘንድ፣ እሊህን ሐሳቦች ለማቅረብ ደፈርን፡፡››