የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋሊያዎቹ) ለአይቮሪኮስት አፍሪካ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ ማጣሪያ ጨዋታ የግብፅ ብሔራዊ ቡድንን (ፈርዖኖች) ይገጥማል፡፡
በምድብ አራት ከግብፅ፣ ጊኒና ማላዊ ጋር የተደለደለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከምድቡ መሰናበቱን ቢያረጋግጥም፣ የምድቡን ስድስተኛ ጨዋታ በግብፅ ካይሮ ስታዲየም ይደረጋል፡፡
ዋሊያዎቹ በቡሩንዲ ስታዲየም በተካሄደው የመጀመርያው የምድብ ጨዋታ ፈርዖኖች 2 ለ0 በሆነ ውጤት መርታት የቻሉ ሲሆን፣ ከጊኒና ማላዊ ጋር ባደረጉት ጨዋታ መሸነፋቸውን ተከትሎ ከምድባቸው ማለፍ አልቻሉም፡፡ በዚህም ምክንያት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከአሠልጣኝ ውበቱ አባተ ጋር የገባውን ውል ማቋረጡ ይታወሳል፡፡
በምትኩም የፌዴሬሽኑን የቴክኒክ ኃላፊ የሆነውን ኢንስትራክተር ዳንኤል ገብረ ማርያምን ጊዜያዊ አሠልጣኝ አድርጎ ሾሟል፡፡
ዋሊያዎቹ በጊዜያዊ አሠልጣኙ መመራት ከጀመሩ በኋላ የምድባቸውን አምስተኛ ጨዋታ ከማላዊ ጋር አድርገው ያለምንም ግብ መለያየታቸው ይታወሳል፡፡
ዓርብ ጳጉሜን 3 ቀን 2015 ዓ.ም. የግብፅ አቻውን የሚገጥመው ብሔራዊ ቡድኑ ለ23 ተጨዋቾች ጥሪ አድርጎ በኢትዮጵያ ስፖርት አካዴሚና በዕድሳት ላይ በሚገኘው የአዲስ አበባ ስታዲየም ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ማክሰኞ ነሐሴ 30 ቀን 2015 ዓ.ም. ከማጣሪያ ጨዋታው ጋር በተያያዘ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አቡበከር ናስር፣ ምኞት ደበበና ቢንያም በላይ ሕክምና ላይ በመሆናቸው ምክንያት ከስብስቡ ውጭ መሆናቸውን አሠልጣኙ አብራርተዋል፡፡
ዋሊያዎቹ ፈርዖኖቹን በሜዳቸው ለመግጠም የተደረገውን ዝግጅት በተመለከተ ለአሠልጣኙ ጥያቄ የቀረበላቸው ሲሆን፣ ‹‹ተጋጣሚያችን ግብፅ ስለሆነ ብለን የተለየ ዝግጅት አላደረግንም፣ ለሁሉም ጨዋታዎች የምናደርገውን ተመሳሳይ ዝግጅት አድርገናል፤›› በማለት አሠልጣኝ ዳንኤል አስረድተዋል፡፡
ከዚህም ባሻገር የሊቨርፑሉ አጥቂ መሐመድ ሳላህ በግብፅ ብሔራዊ ቡድን ውስጥ መኖሩ ሥጋት አይሆንም የሚለው ጥያቄ የተነሳ ሲሆን፣ ቡድኑ በቂ ዝግጅት ማድረጉንና የአንድ ተጨዋች ተፅዕኖ የሚያሠጋ እንደማይሆን አሠልጣኙ አንስተዋል፡፡
በአንፃሩ ዋሊያዎቹ በመጀመርያው የምድብ ጨዋታ ፈርዖኖቹና በመርታታቸው የካይሮ ጨዋታ ተጠባቂ ያደርገዋል፡፡
ያልተጠበቀ ሽንፈት ያስተናገዱት ፈርዖኖቹ በሜዳቸው ‹‹የበቀል በትር›› ለማሳረፍ መሰናዳታቸው እየተነገረ ይገኛል፡፡ ከምድባቸው 12 ነጥብ በመሰብሰብ ቀድሞንም ማለፋቸውን ያረጋገጡ ሲሆን፣ ከዋሊያዎቹ ጋር የሚያደርጉት ጨዋታ ከምንም በላይ የሚጠብቁት እንደሆነ ይገመታል፡፡
ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች የሚያደርጉት ጨዋታ ከእግር ኳስም በላይ ፖለቲካዊ አንድምታ ያለው መሆኑ ተጠባቂ ያደርገዋል፡፡
በተለይ በዚህ ወቅት ኢትዮጵያና ግብፅ በዓባይ ወንዝና ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ እየተወያዩ ባሉበት ሁኔታ መሆኑ ተጠባቂና የበለጠ አጓጊ አድርጎታል፡፡
የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ ማጣሪያ ጨዋታውን የሚያደርገው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን፣ በ2016 በአዲስ አሠልጣኝ አማካይነት በሌሎች የአፍሪካና የዓለም ዋንጫ የማጣሪያ ጨዋታ ይጠበቃል፡፡