- በበጀት ዓመቱ 573 ሚሊዮን ኩንታል ለማምረት ማቀዱን አስታወቀ
በኦሮሚያ ክልል በተወሰኑ ቦታዎች የቲማቲም ማሳቸውን ‹‹ለስንዴ ምርት አውሉት ተብለናል፤›› ያሉ አርሶ አደሮች፣ ማንም እንዳላስገደዳቸውና በራሳቸው ፈቃድ ማሳቸውን ለዚህ ጥቅም ማዋላቸውን በግብርና ሚኒስቴር የእርሻና ሆልቲካልቸራል ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ደኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
እንደ ሚኒስትር ደኤታው ገለጻ ከሆነ፣ አርሶ አደሩ ‹‹ቲማቲም ነቅላችሁ ስንዴ ዝሩ ተባልን›› ብሏል የተባለው፣ በመንግሥት አስገዳጅነት ሳይሆን ራሱ የበለጠ ጥቅም የሚሰጠውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ፈልጎ ያደረገው ሊሆን እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡
ሚኒስቴሩ በ2015 እና 2016 የመኸር ወቅት 573 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ዕቅድ መያዙንም ሚኒስትር ደኤታው ተናግረዋል፡፡
በ2015 እና 2016 የመኸር ምርት ዘመንን አስመልክቶ ነሐሴ 26 ቀን 2015 ዓ.ም. በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተገጸው፣ በኦሮሚያ ክልል በመስኖ፣ በበልግና በመኸር ወቅቶች ከፍተኛ የሆነ የስንዴ ምርት ማምረት መቻሉን መለስ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
በ2015 እና 2016 የመኸር ወቅት 17.3 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በዘር ለመሸፈን መታቀዱን፣ እስካሁንም 15.8 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በዘር መሸፈኑን የግብርና ሚኒስቴር የእርሻና ሆልቲካልቸር ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ደኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
በዘር ከተሸፈነው 15.8 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ውስጥ 7,866 ሚሊዮን ሔክታር መሬት የሚሆነውን በክላስተር ወይም በኩታ ገጠም ማሳ ማልማት መቻሉን ገልጸዋል፡፡
በመኸር፣ በበልግም ሆነ በመስኖ ምርት ወቅት በክልል ደረጃ ሲታይ ሰፊውን ድርሻ የሚወስዱት ኦሮሚያና አማራ ክልሎች መሆናቸውን ሚኒስትር ደኤታው አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል በዘንድሮ የመርኸ ወቅት 3.6 ሔክታር መሬትን በስንዴ ምርት ለመሸፈን መታቀዱን፣ እስካሁንም 2.8 ሔክታር መሬት በዘር መሸፈኑን አብራርተዋል፡፡
ባለፉት ሦስት ዓመታት በአገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የማዳበሪያ አቅርቦት ችግር እንደነበረ፣ ችግሩም በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ጭምር መሆኑን አስታውሰዋል፡፡
በአማራ ክልል ያጋጠመው የማዳበሪያ አቅርቦት ችግር በሌሎች ቦታዎች ላይ መከሰቱን፣ መንግሥት አፋጣኝ የሆነ ምላሽ በመስጠት የማዳበሪያ አቅርቦት ችግርን መፍታት ተችሏል ብለዋል፡፡
ይሁን እንጂ አማራ ክልልን ጨምሮ በሌሎች አካባቢዎች በመንግሥት የተላከው ማዳበሪያ ባለማሠራጨቱ፣ አርሶ አደሮች በፈለጉት ጊዜ ማዳበሪያ ሳያገኙ መቅረታቸውን ጠቁመዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ፆም የሚያድሩ መሬቶችን በዘር ለመሸፈን ከክልሎች ጋር ስምምነት መደረጉን፣ በዚህም ምክንያት በዘር የሚሸፈነው ምርት ሊጨምር እንደሚችል መለሰ (ዶ/ር) አብራርተዋል፡፡
መንግሥት በዚህ ዓመት 21 ቢሊዮን ብር በሆነ ወጪ የማዳበሪያ ግዥ በመፈጸም፣ ለአርሶ አደሮች ማዳበሪያ ማቅረብ መቻሉንም ገልጸዋል፡፡