በ2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባና በዙሪያዋ በተከሰተ የእሳት አደጋ የዘጠኝ ሰዎች ሕይወት ያለፈ ሲሆን፣ በ122 ሰዎች ላይ ከባድና ቀላል ጉዳት መድረሱን፣ የአዲስ አበባ ከተማ እሳትና አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ 495 አደጋዎች ያጋጠሙ መሆኑን፣ ከእነዚህ ውስጥ 326 ያህሉ በእሳት አደጋ የተከሰቱ መሆናቸውን የኮሚሽኑ የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ንጋቱ ማሞ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ ከእሳት ጋር ተያይዞ ከተከሰቱት አደጋዎች ውጪ ያሉት ደግሞ፣ በድንገተኛ አደጋ ያጋጠሙ ክስተቶች መሆናቸውን ባለሙያው አስረድተዋል፡፡
በአደጋው ከሰዎች ሕይወት ማለፍና ከአካል ጉዳት በተጨማሪ፣ 864.4 ሚሊዮን ብር የሚገመት ንብረት ወድሟል ሲሉ አቶ ንጋቱ ጠቁመዋል፡፡
የአደጋ መቆጣጠር ሠራተኞች ባደረጉት ጥረት በአደጋው ጉዳት ሊደርስባችው የነበሩ የ20 ሰዎች ሕይወት ማትረፍ ተችሏል ያሉት ባለሙያው፣ ከ9.8 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ከጉዳት መዳኑን አክለዋል፡፡
ከደረሱት አደጋዎች መካከል የ175 ያህሉ መንስዔ የታወቀ መሆኑን፣ ቀሪዎቹ አደጋዎች ግን በምን ምክንያት እንደተከሰቱ አልታወቀም ሲሉ ባለሙያው ተናግረዋል፡፡
አቃቂ ቃሊቲና ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍላተ ከተሞች ከፍተኛ አደጋ የተመዘገበባቸው መሆናቸውን፣ ቦሌና ቂርቆስ ክፍላተ ከተሞች ደግሞ ዝቅተኛ አደጋ የደረሰባቸው አካባቢዎች ናቸው ብለዋል፡፡
ለአደጋው መከሰት መንስዔ ናቸው ተብለው ከተጠቀሱት ምክንያቶች መካከል ሆቴሎችን ጨምሮ የተለያዩ ፋብሪካዎች፣ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና የገበያ ማዕከላት የአደጋ ደኅንነት መሥፈርት ባለማሟላታቸው የሚከሰቱ አደጋዎች ይገኙበታል ሲሉ አቶ ንጋቱ አስረድተዋል፡፡
ሆቴሎችን ሳይጨምር ከተዘረዘሩ አሥር ሺሕ ከሚሆኑ ተቋማት ውስጥ የአደጋ ደኅንነት ብቃት ማረጋገጫ ወስደው እየሠሩ ያሉት 25 ብቻ ናቸው ያሉት ባለሙያው፣ ከ187 ሆቴሎች መካከል ደግሞ 23 ያህል ብቻ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
የደኅንነት ማረጋገጫ መሥፈርቱን ሳያሟሉ በሚሠሩ ተቋማት ላይ ለምን ቁጥጥር አልተወሰደባቸውም ሪፖርተር ለባለሙያው ባቀረበላቸው ጥያቄ፣ ‹‹እስካሁን ዕርምጃ መውሰድ አልጀመርንም ይህም ትክክል ነው ብለን አናምንም፤›› ያሉ ሲሆን፣ አሁን በአገሪቱ ባለው ነባራዊ ሁኔታና ለደኅንነት የሚሰጠው ግምት ባልዳበረበት ወቅት ወደ ዕርምጃ ብንገባ ምናልባትም ከፍተኛ ቅሬታን ሊያስከትል ስለሚችል ነው ብለዋል፡፡
‹‹ከሁሉም በፊት መመካከሩ ይቀድማል፤›› ያሉት አቶ ንጋቱ፣ የአደጋ ደኅንነት መሥፈርትን አሟልቶ መሥራት አትራፊ ያደርጋል ሲሉ አክለዋል፡፡
ከዚህ ባሻገር የቅጣት መመርያ አለመኖር ዕርምጃ ለመውሰድ እንደሚገድባቸው ገልጸው፣ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት የእሳት አደጋ ቅጣት መመርያ እየተዘጋጀ ነው ብለዋል፡፡ መመርያው እንደተጠናቀቀ ወደ ዕርምጃ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡