አሜሪካ በማሊ የመከላከያ ሚኒስቴር ከፍተኛ ኃላፊዎች ላይ ማዕቀብ ጥላለች፡፡ ማዕቀቡን የጣለችው ደግሞ የሩሲያ መደበኛ ጦር አባል ያልሆነው የዋግነር ቡድን በምዕራብ አፍሪካ እንዲሠራ የማሊ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ሁኔታዎችን አመቻችተዋል በሚል ነው፡፡
አልጀዚራ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒ ብሊንከንን ጠቅሶ እንደዘገበው፣ ገደቡ የተጣለው በማሊ መከላከያ ሚኒስትር ኮሎኔል ሳዲዮ ካማራ፣ የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ኮሎኔል አሎ ቦይ ዴራና በምክትል ዋና አዛዡ ሌተና ኮሎኔል አዳማ ባጋዮኮ ላይ ነው፡፡
የማሊ መከላከያ ሚኒስቴር ባለሥልጣናት፣ እ.ኤ.አ. ከ2021 ጀምሮ የዋግነር ቡድን አባላት በማሊ ሰፊ ሥፍራዎችን እንዲቆጣጠሩ አመቻችተዋል ተብለው ይወቀሳሉ፡፡
የዋግነር ቡድን ማሊ ከገባ በኋላ የንፁኃን ሞት 278 በመቶ የጨመረ ሲሆን፣ አብዛኛው ሞትም የማሊ መከላከያና የዋግነር ቡድን አባላት በጋራ ሆነው በወሰዱት ወታደራዊ ዕርምጃ መሆኑን ብሊንከን ገልጸዋል፡፡
የማሊ ወታደራዊ ባለሥልጣናት የዋግነር ቡድን በአገሪቱ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ከማመቻቸትም ባለፈ፣ ቡድኑ በዩክሬን ለሚያደርገው እንቅስቃሴ የገዛ አገራቸውን ሀብት ያስበዘብዛሉ፣ የዜጎቻቸውን ሰብዓዊ መብት ያስረግጣሉ፣ የሰዎችን እንቅስቃሴ ያስተጓጉላሉ ስትልም አሜሪካ ትከሳለች፡፡
ለዓመታት አሜሪካና አጋሮቿ በዋግነር ቡድንና ቡድኑን በሚደግፉ አካላት ላይ ማዕቀብ ሲጥሉ የቆዩ ሲሆን፣ ባለፈው ሳምንትም እንግሊዝ በማሊና በሱዳን ከቡድኑ ጋር ግንኙነት አላቸው ባለቻቸው 13 ግለሰቦች ላይ ማዕቀብ ጥላለች፡፡
አሜሪካም በግንቦት በማሊ የዋግነር ዋና አዛዥ ነው ባለችው ኢቫን አሌክሳንድሮቪች ማስሎቭ በተባለ ግለሰብ ላይ ማዕቀብ መጣሏ ይታወሳል፡፡
የአሜሪካ ባለሥልጣናት በሩሲያዊው ይቬጌኒይ ፕሪዝኒ የተመሠረተውንና በአፍሪካ በደኅንነት፣ ጥበቃና የተዛባ መረጃ በመንዛት የሩሲያን ፍላጎት ያስብቃል በምትለው ዋግነር ቡድን ላይ ለረዥም ጊዜያት ወቀሳ ሲሰነዝሩ ከርመዋል፡፡
የዋግነር ቡድን በማሊ ወታደራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ብቻ ሳይሆን፣ በአገሪቱ ሰላም ለማስፈን የተሰማራውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ሰላም አስከባሪ ቡድን ከአገሪቱ ለቆ እንዲወጣ አቀነባብሯል በሚልም በአሜሪካ ይወቀሳል፡፡
13 ሺሕ የተመድ ሰላም አስከባሪ አባላት ከማሊ እንዲወጡ የማሊ መንግሥት የጠየቀ ሲሆን፣ ተመድም አባላቱ ከአገሪቱ ለቀው እንዲወጡ ወስኗል፡፡
በማሊ የሚገኘው ሰላም አስከባሪ ቡድን በፈረንጆቹ ዓመት መጨረሻ ሙሉ ለሙሉ ለቆ የሚወጣ ሲሆን፣ ይህ በአገሪቱ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየተባባሰ የመጣውን ጥቃት ያባብሰዋል፣ በድንበር አካባቢ ሚንቀሳቀሰው የአይኤስአይኤስ ቡድን ጫና እንዲያሳድር ይረዳዋል ተብሏል፡፡
ከ2021 ጀምሮ ከማሊ መንግሥት ጋር አብሮ ይሠራል በሚባለው የዋግነር ቡድን፣ የማሊ መንግሥት ፈጽሞታል ለሚባለው የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ የጦር ወንጀልና በሰዎች ላይ ለሚፈጸም ወንጀል ምርመራ እንዲደረግ የተመድ ባለሙያዎች ከአሥር ወራት በፊት መጠየቃቸው ይታወሳል፡፡
የሒዩማን ራይትሰዎች በበኩሉ፣ የማሊ ወታደሮችና የዋግነር ቡድን አባላት በማዕከላዊ ማሊ በርካታ ሰዎችን ገድለዋል ብሏል፡፡
የአሜሪካ ብሔራዊ ደኅንነት ምክር ቤት ቃል አቀባይ ጆን ኪርባይ እንደሚሉትም፣ የማሊ የሽግግር መንግሥት ከ2021 ጀምሮ ለዋግነር ቡድን ከ200 ሚሊዮን ዶላር በላይ ከፍሏል፡፡
እ.ኤ.አ. በ2014 እንደተመሠረተ የሚታመነው የዋግነር ቡድን፣ እ.ኤ.አ. ከ2015 ጀምሮ ከሶሪያ መንግሥት ጎን ተሠልፎ እንደሚዋጋና የነዳጅ ማውጫ አካባቢዎችን እንደሚጠብቅም ምዕራባውያኑ ይናገራሉ፡፡
በሊቢያ ወታደሮች እንዳሉት የሚታመነው ዋግነር፣ በማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ የዳይመንድ፣ በሱዳን ደግሞ የወርቅ ማዕድናት የሚገኙባቸውን ሥፍራዎች እንደሚጠብቅም ይታመናል፡፡
በምዕራብ አፍሪካ የማሊ መንግሥት አይኤስን ለመዋጋት ቡድኑን የሚጠቅም ሲሆን፣ የቡድኑ የገንዘብ ምንጭም በውጭ አገሮች የሚሰጠው የውትድርና አገልግሎት ነው፡፡
ቡድኑ በአፍሪካ ከአሥር ባላነሱ አገሮች ውስጥ የተሰማራ ሲሆን፣ በዩክሬን ጦርነት ከሩሲያ ጎን በመሠለፍ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል።