በኢትዮጵያ ሁለተኛውን የቴሌኮም ፈቃድ በጨረታ አሸንፎ ሥራ የጀመረው ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የ2015 ዓ.ም. የበጀት ዓመት ከጀመረበት ሁለተኛው ወር አጋማሽ አንስቶ በይፋ የዘርፉ ተወዳዳሪ ሆኖ ወደ አገልግሎት በመግባቱ ኢትዮ ቴሌኮም የዘንድሮ የገቢ ግኝቱ እንዴት ይሆናል? የሚለው ከኢትዮ ቴሌኮምን ዓመታዊ የሥራ ክንውን ተጠባቂ ጉዳይ አድርጎታል፡፡
በኢትዮጵያ ሁለተኛውን የቴሌኮም ፈቃድ በጨረታ አሸንፎ ሥራ የጀመረው ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ ትርፍ ለማግኘት ቢያንስ አምስት ዓመታት ሊፈጅበት እንደሚችል ከዚህ ቀደም ያስታወቀ ቢሆንም፣ የመጀመሪያ የሆነውን የቴሌኮም አገልግሎት ካስጀመረበት ነሐሴ 23 ቀን 2014 ዓ.ም. እስከ ግንቦት 2015 ዓ.ም. ያለው የኩባንያው ሥራ አፈጻጸም ቁጥራዊ ዕውነታዎች ከ2.8 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችንና 13 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ያመለክታሉ።
ከላይ የተገለጹት ጉዳዮች እንደተጠበቁ ሆነው ኢትዮ ቴሌኮም በቴሌኮም ውድድር ገበያው የመሪነት ሚናውን እጠናክሮ ለማስቀጠል ያስችለኛል ያለውን ሁለተኛውን የሦስት ዓመት መሪ የዕድገት ስትራቴጂ (LEAD Growth Strategy) ተግባራዊ ማድረግ በጀመረበት የመጀመሪያ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ዘርፈ ብዙ ውጤቶች ያገኘበት መሆኑን በተጠናቀቀው ሳምንት አጋማሽ ይፋ አድርጓል፡፡
ከገቢ፣ አገልግሎትና ደንበኛ አንፃር የቴሌኮም ኩባንያው ምን ያህል ስኬታማ ነበር?
ኢትዮ ቴሌኮም በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከመሠረታዊ ቴሌኮም አገልግሎቶች ባሻገር ከበርካታ ተቋማት ጋር በመሆን የዲጂታል መፍትሔዎች፣ የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎቶች ናቸው ያላቸውን አገልግሎቶች በማቅረብ 75.8 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ በማግኘት የዕቅዱን 101 በመቶ ማሳካቱን ይፋ አድርጓል፡፡
ኩባንያው ያገኘው ገቢ ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ23.5 በመቶ ብልጫ ያለው መሆኑን የተናገሩት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሪት ፍሬሕይወት ታምሩ፣ ለተገኘው ገቢም የድምፅ አገልግሎት 43.7 በመቶ፣ ዳታና ኢንተርኔት 26.6 በመቶ፣ ዓለም አቀፍ ገቢ ዘጠኝ በመቶ፣ እሴት የሚጨምሩ አገልግሎቶች 6.9 በመቶ፣ የቴሌኮም መጠቀሚያ መሣሪያዎች (ቀፎ፣ ዶንግል፣ ሞደም) 4.7 በመቶ እንዲሁም ሌሎች አገልግሎቶች 7.2 በመቶ ድርሻ እንደነበራቸው ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል ገበያውን የተቆጣጠረው ኢትዮ ቴሌኮም መሠረተ ልማቱን በማከራየት ዘንድሮ ካገኘው አጠቃላይ ገቢ አንድ በመቶ የሚሆነውን ገቢ ከተወዳዳሪው አግኝቷል፡፡ በዚህም መሠረት ኢትዮ ቴሌኮም ዘንድሮ ካገኘው 75.8 ቢሊዮን ብር ውስጥ 758 ሚሊዮን ብር የሚሆነውን ያገኘው ከሳፋሪ ኮም የመሠረተ ልማት ኪራይ ክፍያ መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም በ2015 በጀት ዓመት አጠቃላይ ካገኘው 75.8 ቢሊዮን ብር ገቢ ውስጥ 18.78 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ከኦዲት በፊት የተጣራ ትርፍ መሆኑም ተገልጿል፡፡
በ2014 የበጀት ዓመት የነበረው የኩባንያው ትርፍ 8.99 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት የተመዘገበው የተጣራ ትርፍ 25 በመቶ ዕድገት ያለው ነው፡፡ ኩባንያው በወድድር ገበያ ውስጥ ሆኖ ባሳለፈው የበጀት ዓመት ያገኘው መልከ ብዙ ስኬትና ውጤት በውድድር ገበያ ደንበኞችን ለማቆየት በተሠራው ሥራ የመጣ መሆኑን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ ተናግረዋል።
‹‹በበጀት ዓመቱ 203 የሚሆኑ አዳዲስና የተሻሻሉ አገልግሎቶችን በማቅረብ 75.8 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኝት ችለናል፡፡ በዕውነቱ ዛሬ ላይ ሆኖ ይሄንን አሳክተናል ብሎ መናገር ቀላል ነገር ይመስላል፡፡ የበጀት ዓመቱ ግን በርካታ ውጣ ውረዶች የነበሩበት፣ በርካታ ፈታኝ ሁኔታ ውስጥ የነበረበት ዓመት ነው፤›› ያሉት ወ/ት ፍሬሕይወት፣ ‹‹ይኼንን ገቢ ያገኘነው ደግሞ በውድድር ገበያ ሆነን እንደዚሁም ለደንበኞቻችን ርካሽ የሚባል አገልግሎቶችን በማቅረብ ጭምር ነው፤›› ሲሉ አፈጻጸሙን አሞካሽተዋል፡፡
በተጨማሪም ኩባንያው የውጭ ምንዛሪ ከሚያስገኙ አገልግሎቶች ማለትም ከዓለም አቀፍ የቴሌኮም ግንኙነት ሮሚንግ፣ ከመሠረተ ልማት ኪራይና ከሐዋላ አገልግሎቶች አጠቃላይ 164.1 ሚሊዮን ዶላር ያገኘ ሲሆን፣ ይህም የዕቅዱ 107.8 በመቶ የተፈጸመበት ነው ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ በማሰብ የተጀመረው ‹‹የቴሌ ብር›› የሞባይል ገንዘብ ዝውውር አገልግሎት 34.3 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን አፍርቶ አጠቃላይ በኢኮኖሚው ላይ ያገላበጠው የግብይት መጠን (Transaction Value) 679.2 ቢሊዮን ብር እንደደረሰ ኩባንያው አስታውቋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም ከገቢ አንፃር በበጀት ዓመቱ ያገኘው ገቢ በውጭ ምንዛሪ ሲሰላ አጠቃላይ ገቢው 1.37 ቢሊዮን ዶላር፣ ትርፉ 340 ሚሊዮን ዶላር፣ የቴሌ ብር ግብይት መጠኑ 12.2 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም ሌሎች የውጭ ምንዛሬ ከሚያገኝባቸው ዓለም አቀፍ አገልግሎቶች ያገኘው የውጭ ምንዛሬ ደግሞ 164 ሚሊዮን ዶላር መሆኑን ፌር ፋክስ የኢትዮ ቴሌኮም ምንጭን ጠቅሶ ያቀረበው አኃዝ ያስረዳል፡፡
በ2015 የበጀት ዓመት የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ደንበኞቹን ብዛት 72 ሚሊዮን አድርሻለሁ ያለው ኢትዮ ቴሌኮም፣ አምና በመሳሳይ ወቅት ከነበረው የደንበኞቹ ቁጥር የስምንት በመቶ ዕድገት እንዳገኘ፣ ከዚህም ውስጥ የሞባይል ድምፅ ደንበኞቹ ብዛት 69.5 ሚሊዮን፣ የመደበኛ ብሮድባንድ (Fixed Broadband) ደንበኞቹ 618.3 ሺሕ፣ የመደበኛ ስልክ ደንበኞች 853.6 ሺሕ እንዲሁም የዳታና ኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 33.9 ሚሊዮን መድረሱን ገልጿል፡፡
ከገቢ ባሻገር ኩባንያው በበጀት ዓመቱ ለተለያዩ ወጪዎች 82.2 ቢሊዮን ብር ፈሰስ ማድረጉን አስታውቋል፡፡ ለታክስ 20.8 ቢሊዮን ብር፣ ለብድር 4.23 ቢሊዮን ብር (78.4 ሚሊዮን ዶላር)፣ ለትርፍ ክፍፍል (ለዲቪደንድ) 2.5 ቢሊዮን ብር፣ እንዲሁም ለመደበኛና ለካፒታል በጀት ወጪና ለሌሎች ወጪዎች 54.6 ቢሊዮን ብር ክፍያ አከናውኛለሁ ብሏል፡፡
የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሪት ፍሬሕይወት ታምሩ ማክሰኞ ሐምሌ 11 ቀን 2015 ዓ.ም. የተቋማቸውን የ2015 የበጀት አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት በሪፖርተር ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች ውስጥ ኩባንያው በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በተለይም ጉዳት በደረሰባቸው የትግራይ፣ የአፋርና የአማራ አካባቢዎች የወደሙ የቴሌኮም መሠረተ ልማቶችን እንደገና ወደ ሥራ ለመመለስ ምን ያህል ወጪ አወጣ? የውድመቱስ መጠን ምን ያህል ነው? የሚሉት ይገኝበታል፡፡
በተጨማሪም የኢትዮጵያን የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት ፍላጎት ለማርካትና የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ በቀረበው የቴሌ ብር አገልግሎት እስካሁን ኩባንያው ያፈራቸውን ደንበኞች ቁጥር፣ ምን ያህል ገንዘብ እንደተንቀሳቀሰ ከመግለጽ ውጪ ከዚህ አገልግሎት ተቋሙ ያገኘው ገቢና ትርፍ ምን ያህል ነው? የሚለው ሌላው ጥያቄ ነበር፡፡
ምንም እንኳን ከላይ በሁለተኛ ደረጃ ለተነሳው ጥያቄ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ የሰጡት ቀጥተኛ መልስ ባይኖርም፣ ሪፖርተር የተመለከተው የኩባንያው ሥራ አፈጻጸም ሰነድ እንደሚያሳየው፣ ከተጀመረ ሁለት ዓመታት የሆነው የቴሌ ብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት 34.3 ሚሊዮን ደንበኞችን እንዳፈራ፣ እስካሁንም የተከናወነበት የግብይት መጠን 679.2 ቢሊዮን ብር መድረሱንና በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከኩባንያው ካገኘው አጠቃላይ ገቢ ውስጥ የቴሌ ብር አገልግሎት 0.9 በመቶ ወይም 682.2 ሚሊዮን ብር ድርሻ መያዙን ለማወቅ ተችሏል፡፡
አማራጭ የፋይናንስ ቁጠባና ብድር አገልግሎትን ከዳሽንና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች ጋር በመሆን ማቅረብ መጀመሩንና በዚህም ጥሩ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አንዳንድ የብድር አማራጮች ላይ የሚጠየቀው የአገልግሎት ክፍያ እስከ 21 በመቶ ከፍ ማለቱ ለዝቅተኛው ማኅበረሰብ የፋይናንስ አማራጭ ለማድረስ ከሚለው ዕሳቤ ጋር እንዴት ይጣጣማል? በማለት ሪፖርተር ላቀረበው ጥያቄ ወ/ሪት ፍሬሕይወት በሰጡት ምላሽ፣ ሥራው ከባንኮቹ ጋር በመሆን እንደሚሠራ፣ ኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል ፋይናንስ አገልግሎት ለመስጠት የራሱን ፋይናንስ ቀጥታ መጠቀም እንደማይቻልና ሕጉ የሚፈቅድለት ከባንኮች ጋር አብሮ መሥራትን እንደሆነ አስታውሰው፣ የአገልግሎት ክፍያ ሲቀመጥ አብረው ከሚሠሩት ተቋማት ጋር በጋራ በመሆን እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
አገልግሎቱ ያለመያዣ፣ ወደ አገልግሎት መስጫ ጣቢያ ሳይመጣና ደንበኛው ምንም ዓይነት ኮንትራት ሳይፈራረም የሚሰጥ በመሆኑ መጀመሪያ ላይ መላመድ የሚጠይቅ እንደሆነ፣ ነገር ግን እየተለመደና ባህል እየሆነ ሲመጣ ተያያዥነት ያላቸው ወጪዎች እየቀነሱ እንደሚመጡ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አክለዋል፡፡
የብዙ ዜጎች ሕልፈት መንስዔ ሆኖ ያለፈው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ካደረሰው የሰብዓዊ ጉዳት ባሻገር በመሠረተ ልማት ሀብቶች ላይ ያደረሰው ውድመት ከፍተኛና መልሶ ለመተካት ጊዜያትን የሚፈልግ መሆኑ ዕሙን ነው፡፡ በተለይም በከፍተኛ ወጪ የተዘረጉ የቴሌኮም መሠረተ ልማት ውድመቶች በመከሰታቸው የሞባይል አገልግሎት ጣቢያዎች መጎዳታቸውን ብሎም መውደማቸውን፣ የቴሌኮም ምሰሶች መጠቃታቸውን፣ የፋይበር መስመሮች ላይ ጉዳት መድረሱን አንጋፋው የመንግሥት የቴሌኮም ልማት ኩባንያ ኢትዮ ቴሌኮም በተደጋጋሚ ሲገልጽ ቆይቷል፡፡
ከፕሪቶሪያው ስምምነት በኋላ፣ እንዲሁም ጦርነት ውስጥ የቆዩ አካባቢዎች የቴሌኮም አገልግሎቶችን አንፃራዊ በሆነ መንገድ ዳግም ካገኙ በኋላ ኩባንያው በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በተለይም ጉዳት በደረሰባቸው የትግራይ፣ የአፋርና የአማራ አካባቢዎች የወደሙ የቴሌኮም መሠረተ ልማቶችን እንደገና ወደ ሥራ ለማስገባት ከፍተኛ ወጪ እንዳወጣ ያስታወቀ ሲሆን፣ በተጨማሪም ለሌሎች የማስፋፊያ ፕሮጀክቶቹ ያሰባቸውን ግብዓቶች ወደ እነዚህ አካባቢዎች ለማዞር መገደዱን ኩባንያው ገልጾ ነበር፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎቱን ለመመለስ ያወጣው ወጪ፣ የደረሰው የቴሌኮም መሠረተ ልማት ውድመት ብቻ ሳይሆን የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነትና በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች የነበረው የፀጥታ ችግሮች በኩባንያው የሥራ አፈጻጸምና የገቢ ግኝት ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል ብለው ሙያዊ አስተያየታቸውን ሲሰጡ የቆዩ ዘርፉን በቅርበት የሚከታተሉ ባለሙያዎች የኩባንያውን የበጀት ዓመት አጠቃላይ እንቅስቃሴ በአንክሮ ስለመከታተላቸው ይናገራሉ፡፡
በሰሜኑ ኢትዮጵያ ክፍል ብቻ ሳይሆን በአገሪቱ ምዕራብ ክፍል ባሉ አካባቢዎች ጉዳት የደረሰባቸውን የቴሌኮም መሠረተ ልማት ውድመቶችን በመጠገን ወደ ሥራ እየመለሰ እንደሚገኝ ያስታወቀው ኢትዮ ቴሌኮም፣ በተያዘው የበጀት ዓመት በፀጥታ ችግር ምክንያት አገልግሎታቸው ተቋርጦ የነበሩ 943 የሞባይል ጣቢያዎች እንደተጠገኑ፣ በዚህም ምክንያት 86 ከተሞችና ወረዳዎች አገልግሎት እንዳገኙ፣ 1,886 ኪሎ ሜትር የፋይበር ኬብል ጥገና እንደተከናወነ፣ በዚህም በ20 ዋና ዋና ከተሞች የሚገኙ 22 የአገልግሎት ጣቢያዎች ተመልሰው ወደ ሥራ መግባታቸው ተገልጿል፡፡
የ2015 የበጀት ዓመት በአገሪቱ በቴሌኮም ገበያው አዳዲስ ልምምዶች የተስተዋሉበት ሲሆን፣ በዚህም ለቴሌኮም አገልግሎት ተጠቃሚዎች በዘርፉ ከተፈጠረው የገበያ ውድድር ዘርፈ ብዙ አማራጮችን መርጠው እንዲወዳጁ እያደረገ ነው፡፡
የዘርፉ ተዋንያንም የሚያደርጉት ፉክክር በቀጣዮቹ ዓመታት እየጋመ እንደሚሄድ የሚናገሩት ዘርፉን የሚከታተሉ ባለሙያዎች በድምፅና በዳታ አገልግሎቶች ላይ በቀረቡት የአገልግሎት አማራጮች በቅርቡ ደግሞ በሞባይል ገንዘብ ዝውውር አገልግሎቶች እንደሚቀርብ አስረጅ በማቅረብ ነው፡፡