በሱዳን መከላከያና የፈጥኖ ደራሽ ኃይል መካከል ከሦስት ወራት በፊት የተጀመረውን ጦርነት በሰላም ለመቋጨት ጥረት ቢጀመርም፣ የፈጥኖ ደራሽ ቡድኑ በደቡብ ዳርፉር፣ የምትገኘውን ካስ ከተማ መቆጣጠሩን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በሺዎች የሚቆጠሩ የካስ ከተማ ነዋሪዎችም ከተማዋን እየለቀቁ ሲሆን፣ የፈጥኖ ደራሽ ቡድኑም የመንግሥት ሕንፃዎችንና ገበያዎችን እያወደመና ዘረፋ እየፈጸመ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ሰላሟ በተናጋውና ካለፉት ሦስት ወራት ጀምሮ በርስ በርስ ጦርነት ውስጥ በገባችው ሱዳን፣ ቀድሞውንም የጦርነት ሰለባ የነበሩት የዳርፉር ነዋሪዎች ይበልጥ ተጠቂ መሆናቸውንም ቢቢሲ ገልጿል፡፡
ከሚያዝያ 2015 ዓ.ም. ወዲህ የዓረብ ማኅበረሰብ ያልሆኑትና በዳርፉር የሚኖሩ ሱዳናውያን በፈጥኖ ደራሽ ቡድኑና በዓረብ ታጣቂዎች ዒላማ መዳረጋቸውንም አትቷል፡፡
በካርቱምና በሱዳን የተለያዩ ከተሞች ውጊያው እንደቀጠለ ሲሆን፣ የርስ በርስ ጦርነቱን በሰላማዊ መንገድ ለመቋጨት ጥረት ተጀምሯል፡፡
በጄኔራል አብዱል ፈታህ አል ቡርሃንና በጄኔራል መሐመድ ሃምዶን ዳጋሎ መካከል የተፈጠረው የሥልጣን ሽሚያ የቀሰቀሰውን ጦርነት ለማርገብ የአፍሪካ ኅብረት፣ የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥት (ኢጋድ) እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) ከጀመሩት እንቅስቃሴ በተጨማሪ በግብፅ ከዓረብ ሊግ አገሮች ጋር በመሆን እንቅስቃሴ የጀመሩ ቢሆንም፣ የሱዳን ተፋላሚ ኃይሎች እጃቸውን ከጥቃት አላነሱም፡፡
ባለፉት ወራትም በሺዎች የሚቆጠሩ ተገድለዋል፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተፈናቅለዋል፡፡
ዘጋርዲያን እንደሚለውም፣ ምንም ማቆሚያ የሌለው በሚመስለው የሱዳን ጦርነት፣ በተለይ ሰለባ በሆኑት የዳርፉር ነዋሪዎች 87 ሰዎች በአንድ ላይ ተቀብረው ተገኝተዋል፡፡ ባለፉት ወራት ብቻ 3.1 ሚሊዮን ሱዳናውያን ከቀዬአቸው የተፈናቀሉ ሲሆን፣ ከግጭቱ ጋር ተያይዞም ፆታዊ ጥቃት ስለመፈጸሙ ለተመድ ኤጀንሲዎች ሪፖርት ደርሷል፡፡
በሱዳን የርስ በርስ ጦርነት ከነዋሪዎች መፈናቀል፣ ከንብረቶች ወይም፣ ከሰዎች መሞትና መቁሰል እንዲሁም ከፆታዊ ጥቃት ባሻገር የሱዳን አርሶ አደሮች፣ የዘሩትን እንኳን ለማጨድ አለመቻላቸውም ታውቋል፡፡
በተለያዩ የሱዳን ክፍሎች የሚገኙ አርሶ አደሮች ሰብል ለመሰብሰብ አለመቻላቸው በጦርነቱ ላይ የከፋ ረሃብና ድህነት ያስከትላልም ተብሏል፡፡
የሱዳን አርሶ አደሮች የሚገኙበት ሁኔታ የረሃብ ቀውሱን ተመድና ዕርዳታ ሰጪዎች ከተነበዩትም በላይ እንደሚሆን ሮይተርስ አስፍሯል፡፡
ተመድ እንደሚለው፣ በሱዳን በነሐሴ 2015 የረሃብተኛ ቁጥር ከጦርነት በፊት ከነበረበት 16.2 ሚሊዮን ወደ 19.1 ሚሊዮን ያሻቅባል፡፡
አርሶ አደሮች ሰብል ካለመሰብሰባቸው ባሻገር ከካርቱም የሚገኙ የእህል መጋዘኖች በመዘረፋቸው ችግሩ የባሰ ያደርገዋል፡፡
ሱዳንን ለሠላሳ ዓመታት የመሯት የቀድሞው የሱዳን ፕሬዚዳንት ኦማር አል በሽር በሚያዝያ 2011 ዓ.ም. በመፈንቅለ መንግሥት ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ ሱዳናውያን በፈለጉት መሪ የመተዳደርም ሆነ ሰላም የማግኘት ዕድል አላገኙም፡፡
በሽር ከሥልጣን እንዲወርዱ ምሁራንን ጨምሮ የተለያዩ የሲቪል ማኅበረሰብ አባላት፣ የዴሞክራሲ አቀንቃኞች፣ ፖለቲከኞችና መከላከያው የተሳተፉበት አብዮት ቢካሄድም፣ ዛሬም ሱዳናውያን በሲቪል መንግሥት እንተዳደር የሚለው ጥያቄያቸው አልተመለሰም፡፡
በሽር ከሥልጣን ከተነሱ ማግሥት ጀምሮ በሱዳን መከላከያና በሲቪሎች በኩል የነበረው ሽኩቻ፣ ሱዳን በሁለቱ ጥምረት እንድትመራ፣ ጥምር የሽግግር መንግሥቱም አጠቃላይ ምርጫ አድርጎ በሱዳን የሲቪል መንግሥት ሥልጣን እንዲቆጣጠር እንዲያደርግ ከስምምነት ተደርሶ የነበረ ቢሆንም አልተሳካም፡፡
‹‹የቀድሞው የሱዳን ፕሬዚዳንት አልበሽርን በመገርሰስ የተጀመረው አብዮታችን ግቡን እስኪመታ ድረስ ተቃውሟችን ይቀጥላል፤›› የሚሉት ሲቪሎች፣ ነፃነትና ሰላም፣ ፍትሕ፣ ሲቪል አገዛዝ እንዲሰፍንና መከላከያው ወደ ካምፑ እንዲገባ እንደሚፈልጉ ሲወተውቱ ቢከርሙም፣ እስካሁን ምላሽ አላገኙም፡፡
የሱዳን መከላከያን በሚመሩት የሱዳን ሉዓላዊ ምክር ቤት ሊቀመንበር ጄኔራል አብዱል ፈታህ አል ቡርሃንና ፈጥኖ ደራሽ ኃይሉን በሚመሩትና ሄሜቲ በሚል ስማቸው በሚታወቁት ጄኔራል መሐመድ ሃምዳን ዳጋሎ መካከል ሚያዝያ 7 ቀን 2015 ዓ.ም. የተጀመረው ጦርነት ይልቁንም ሱዳንን የጦር አውድማ አድርጓታል፡፡