የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የአገሪቱ የሰላምና የኑሮ ውድነት ሁኔታ የከፋ ቀውስ ውስጥ መሆኑንና አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን አስመልክቶ፣ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የሰጠውን መገለጫ ተቃውመው፣ መግለጫ የሰጡ የፖለቲካ ፓርቲዎችን እከሳለሁ አለ፡፡
የጋራ ምክር ቤቱ ሰኔ 2 ቀን 2015 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ፣ በአገራዊ ጉዳዮች ላይ በጠቅላላ ጉባዔ ውይይት ተደርጎ በጉባዔው ውሳኔ ተደርሶባቸዋል ባላቸው ነጥቦች ላይ መግለጫ መስጠቱ ይታወሳል፡፡
ይሁን እንጂ ‹‹የምክር ቤቱ ሥራ አስፈጻሚ የሰጠው ጋዜጣው መግለጫ መርህን ያልተከተለ ነው›› ሲሉ የተወሰኑ ፓርቲዎች ወቀሳ አቅርበዋል፡፡ የተቃውሞ መግለጫ የሰጡት ፓርቲዎች ቁጥራቸው ያልተረጋገጠ ነገር ግን ‹‹32›› መሆናቸውን በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡ ፓርቲዎች፣ የምክር ቤቱ መግለጫ የአባላትን እምነት የሚሸረሽር መሆኑን፣ ምክር ቤቱ የተሰጠውን ኃላፊነት ባለመወጣት በፓርቲዎች መካከል አለመግባባትን የሚፈጥር፣ እንዲሁም ግንኙነቶችን የሚሸረሽር ነው በሚል ሰኔ 7 ቀን 2016 ዓ.ም. ነበር ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥቷል፡፡
ይሁን እንጂ ኢሕአፓ በመግለጫው ‹‹ፓርቲያችን በሌሉበትና ባልመከሩበት የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትን መግለጫ እንደተቃወምን አስመስሎ በሸራተን ሆቴል በሰኔ 7 ቀን 2015 ዓ.ም. ቁጥራቸው ጥቂት የሆኑ ፓርቲዎች ባደረጉት ስብሰባና ባወጡት የአቋም መግለጫ፣ ኢሕአፓ በመግለጫው ላይ እንደተሳተፈ አስመስሎ ስማችንን ማካተታቸውን አጥብቀን እንቃወማለን፤›› ብሏል፡፡
‹‹ይህን ዘመናትን የተሻገረ የሕዝብ ጥያቄ እስኪመለስ ድረስ በጽናት እየታገለ ያለን ፓርቲ ጥላሸት ለመቀባት፣ በድፍረት የተሰባሰቡ ክፍሎች ከዚህ እኩይ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ›› የጠየቀው ፓርቲው፣ ለፈጸሙትም ከፍተኛ ስህተት በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቁ በአጽንኦት ያሳሰበ ሲሆን ይህን የማይፈጸሙ ከሆነ በሕግ ለመጠየቅ እንደሚገደድ አስታውቋል፡፡
‹‹መግለጫውን በማመን በፓርቲው አቋም ላይ ጥርጣሬ የገባችሁ አባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም ተባባሪዎቻችን እውነቱን ተረድታችሁ ከጎናችን ቁሙ፤›› ሲልም ኢሕአፓ ጠይቋል፡፡