- ክቡር ሚኒስትር ካሰባሰብነው መረጃ መረዳት የቻልነው በጀመርነው የስንዴ ልማት ስኬታማ መሆናችን ያልገመትነው ዓለም አቀፍ ፖለቲካ ትግል ውስጥ እየከተተን ነው።
- እንዲቀርብልኝ የጠየኩት መረጃ እኮ ተፈጸመ ስለተባለው የዕርዳታ ስንዴ ምዝበራ ነው?
- አዎ።
- ታዲያ፣ እየተናገርክ ያለኸው ስለመንግሥት የስንዴ ልማት መሆኑን አስተውለሃል?
- ሁሉም ነገር ከጀመርነው የስንዴ ልማት ጋር የሚገናኝ ነው ክቡር ሚኒስትር።
- እንዴት?
- እርስዎ የስንዴ ኤክስፖርት እንዲጀመር ይፋ ማድረግዎትን ተከትሎ ይኸው የአሜሪካ ድርጅት ለኢትዮጵያ ተረጂዎች 300 ሺሕ ኩንታል ስንዴ ከዩክሬን መግዛቱን ገልጾ ነበር።
- ታዲያ መግለጹ ምን ችግር አለው?
- መግለጹ ሳይሆን ከጀርባ ያለው ዓላማ ነው ችግሩ። ዓላማው ደግሞ ዜጎቿን ከዕርዳታ ሳታወጣ ስንዴ ኤክስፖርት ለማድረግ ያቀደች አገር ማሰኘትና የኢትዮጵያን ስም ማጠልሸት ነው።
- ቢሆንም እኛን በዕቅዳችን ከመንቀሳቀስ አላደናቀፈንም።
- ቢሆንም አሁን የተነዛው የዕርዳታ ምዝበራ ተዓማኒነት መደላድል መፍጠር የጀመረው ከዚያ ጊዜ አንስቶ መሆኑን ያሳያል።
- ቀጥል እስኪ።
- የሚገርመው ለኢትዮጵያ ተረጂዎች ከዩክሬን ተገዛ የሚለው የስንዴ መጠን የአንድ ፋብሪካን ዓመታዊ ፍላጎት እንኳ የማያሞላ ሆኖ ሳለ ወሬው ግን ከልክ ያለፈ ነበር።
- ከልክ ያለፈ ነበር ማለት?
- ባልተለመደ መልኩ ስመ ጥር ዓለም አቀፍ የዜና አውታሮች ለኢትዮጵያ ዕርዳታ የጫነች አንድ መርከብ ከዩክሬን ልተነሳ መሆኑን፣ በኋላም ጉዞ መጀመሯን፣ ቀጥሎም ጂቡቲ ወደብ መድረሷን ሲዘግቡ ነበር።
- ሰፋ ያለ ዘመቻ ተከፍቶብን ነበር ነው የምለው?
- በትክክል። ቢሆንም ግን የስም ማጠልሸት ዘመቻ ቸል በማለት ስንዴ ኤክስፖርት የማድረግ ዕቅዳችንን በመተግበር፣ አንዲያውም ለዚሁ የረድኤት ድርጅትና ሌሎች መሰል ድርጅቶች ለአገር ውስጥ የሚያቀርቡትን ስንዴ ከአገር ውስጥ እንዲሸምቱ አደረግን።
- በጣም ጥሩ ነው። ምን ያህል ገዙ?
- የረድኤት ድርጅቶችና የተወሰኑ ዱቄት ፋብሪካዎች 2.9 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ግዥ ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር ተዋውለው እየቀረበላቸው ነው።
- ኤክስፖርቱስ?
- ወደ ሱዳን፣ ኬንያና ሌሎች አራት አገሮች ደግሞ ሦስት ሚሊየን ኩንታል ስንዴ ኤክስፖርት ለማድረግ ውል ተፈጸሟል።
- ጥሩ ነው።
- አዎ። ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ 1.3 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ኤክስፖርት ተደርጓል።
- ታዲያ ለምን በዕርዳታ ሰንዴ ምዝበራ ልንወነጀል ቻልን? የተመዘበረ ነገር የለም ነው የምትለው?
- አይደለም።
- እህሳ …ምንድነው የተፈጠረው?
- አንደኛ ዕርዳታው ለተረጂዎች መድረስ አለመድረሱን የማረጋገጥ ኃላፊነት የራሳቸው ነው። ሁለተኛ በሰሜኑ አካባቢ የተፈጸመውን ሰፋ ያለ የዕርዳታ ምዝበራ ያጋለጠው ራሱ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ቢሆንም የተለያዩ ሸፍጦች ተቀምረው ውንጀላው ወደ መንግሥት እንዲዞር ተደርጓል።
- እንዴት?
- ምክንያቱም በሰሜኑ ክፍል የነበረውን የዕርዳታ ምዝበራ ያረጋገጠው ድርጅቱ አንድም ቦታ የፌዴራል መንግሥትን ተጠያቂ አላደረገም።
- የድርጅቱን ኃላፊ አነጋግራችኋል?
- ኃላፊውን ባናገኝም መረጃዎችን አግኝተናል። ኃላፊውን አግኝተናቸው ቢሆን ጥሩ ነበር።
- ለምን ማግኘት አልቻላችሁም።
- ይህንኑ መረጃ በማውጣታቸው ምክንያት ከኃላፊነት ተነስተዋል።
- ምን?
- አዎ። ኃላፊውን ካነሱ በኋላ ነው ውንጀላውን ወደ መንግሥት እንዲያነጣጥር ያደረጉት።
- ምንድነው ፍላጎታቸው?
- ለፖለቲካቸው እጅ የማትሰጥ ኢትዮጵያ ተፈጥራ ከሚመለከቱ ችጋራምና ደካማ ሆና ብትቀር ይመርጣሉ። ሌላው ሊፈጥር የሚችለውን ቀጣናዊ ተፅዕኖ ማኮላሸት ነው።
- ቀጣናዊ ተፅዕኖ ማለት?
- ኢትዮጵያ በስንዴ ኤክስፖርት ስኬታማ መሆን በመላው አፍሪካ አኅጉርና ከዚያ አልፎ የሚፈጥረውን መነቃቃት ምዕራባዊያኑ በበጎ አይመለከቱትም። ለዚህ ደግሞ የአፍሪካ መንግሥታት የዩክሬንን ጦርነት ተቃውሞ እንዲቆም ለማድረግ የሚወተውቱት በዩክሬን ስንዴ ነው። ሌላው…
- እሺ ቀጥል…
- ኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ስኬቷን አስቀጥላ የጎረቤት አገሮችን ገበያ ከተቆጣጠረች በቀጣናው ለስንዴ ዕርዳታ የማይንበረከክ የተደራጀ የጋራ ፖለቲካዊ አቅም ይፈጠራል ብለው ይሠጋሉ።
- ስለዚህ?
- ስለዚህ ስንዴን አስታኮ የተከፈተው ዘመቻ የዚሁ ፖለቲካ አካል ነው።
- እና ምን መደረግ አለበት ትላለህ?
- የስንዴ ጉዳይ ፖለቲካዊ መሆኑን ተረድተን ዕርዳታ በቃን ሳንል እየተቀበልን በተቃራኒው ደግሞ ስንዴ ወደ ውጭ መላካችንን መቀጠል አለብን። መጋፈጥ ሳይሆን ስልታዊ አጥቂ መሆን ያስፈልጋል። ለምሳሌ….
- ለምሳሌ ምን?
- ለምሳሌ ለአገር ውስጥ ዕርዳታ ብለው ከመንግሥት የገዙትን ስንዴ ከታለመለት ዓላማ ውጪ እንዳይጠቀሙበት ማድረግ አለብን።
- ለምን?
- በኢትዮጵያ ተረጂዎች ስም የገዙትን ስንዴ ሰበብ ፈጥረው ወደ ሌላ አገር የሚያሻግሩ ከሆነ የዕርዳታቸው ተገዢ ያደርጉናል። ስለዚህ ለአገር ውስጥ ተረጂዎች የገዙትን ከታለመለት ዓላማ ውጪ እንዳያውሉት በውል ማሰር አለብን።
- Advertisment -
- Advertisment -