Sunday, September 24, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናበትግራይ በከፋ ረሃብ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱ ተነገረ

በትግራይ በከፋ ረሃብ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱ ተነገረ

ቀን:

በትግራይ ክልል በተራዘመ በምግብ እጦት የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር እየጨመረና ረሃቡ በከፍኛ ሁኔታ እየተባባሰ መምጣቱ ተገለጸ፡፡

ከመቀሌ 40 ኪሎ ሜትር በስተደቡብ በምትገኘው ሳምር ወረዳ ብቻ ባለፉት አራት ወራት 25 ሰዎች የሞቱ ሲሆን፣ በአሁኑ ሰዓት 670 ሕፃናት በአሥጊ ሁኔታ ላይ መሆናቸውም ተጠቁሟል፡፡

ሪፖርተር በአካባቢው ተገኝቶ እንደተመለከተው ብዙ እናቶችና ሕፃናት ያለምግብ በየቤታቸው ተኝተው መንቀሳቀስ አለመቻላቸውን ታዝቧል፡፡

የሳምር ወረዳ ጤና ጽሕፈት ቤት የጤና ኤክስቴንሽን ፓኬጅ ኃላፊ አቶ ጎይቶም ገብሬ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ‹‹ችግሩ እየተባባሰ የመጣው የዕርዳታ አቅርቦት በተለይ ከጥር ወር ወዲህ በመቋረጡ ነው፡፡ ‹‹ከመንግሥት የጠየቅነው ለወራት ምላሽ አላገኘም፡፡ ከምግብ እጥረቱ ጋር በተያያዘ አተት፣ የእናቶች የደም እጥረትና የተለያዩ በሽታዎች እየጨመሩ ነው፡፡ የተረጋገጠና በረሃብ የሞተ ሰው ቁጥር 25 ደርሷል፡፡ ምግብና መድኃኒት በጀት የለም፤›› ብለዋል፡፡

በተመሳሳይ ከመቀሌ 80 ኪሎ ሜትር በስተሰሜን በምትገኘው ተንቤን ከተማ (አቢ አዲ) ከዚህ የከፋ ችግር መኖሩን ሪፖርተር ተመልክቷል፡፡ በተለይ በተንቤን ከተማ 50 ሺሕ አካባቢ ተፈናቃዮች በመኖራቸው ችግሩን የከፋ አድርጎታል፡፡

በተንቤን ከተማ በሚገኘው አንድ ትምህርት ቤት ውስጥ ከተጠለሉት ወደ አሥር ሺሕ የሚጠጉት ተፈናቃዮች ውስጥ 19 ሰው በረሃብ የሞተ ሲሆን፣ ፈተናቃዮቹ ያለ ምንም ዕርዳታ ለወራት መቆየታቸውን ሪፖርተር ያነጋገራቸው ተፈናቃዮች ተናግረዋል፡፡

‹‹በረሃብ የሚሞት ሰው የተረጋገጠ 19 ነው፡፡ ስኳር በሽታ፣ ደም ግፊትና ሌሎች በሽታዎች ያለ ሕክምና ቀርተዋል፡፡ ምንም ዓይነት አቅርቦት የለም፤›› ሲሉ አቶ ታደሰ ይልማ በተንቤን የተፈናቃዮች አስተባባሪ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

የተንቤን (አቢ አዲ) ጤና ጣቢያ ኃላፊ አታክልቲ ገብረ ሕይወት በየቀኑ ከ50 በላይ ሕመምተኛ ቢመጣም ምንም ዓይነት ሕክምና ለመስጠት አልተቻለም ብለዋል፡፡ ወደ መቀሌ ለመላክም አምቡላንሶች እንደሌሉ ተናግረዋል፡፡

በተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች በተለይም ለመቀሌ ቅርብ ቢሆኑም በተራዘመ ረሃብ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ከፍ እያለ በመምጣቱና ችግሩ ከቁጥጥር ውጭ እየወጣ ቢመጣም ከጊዜያዊ አስተዳደሩ ምንም ምላሽ እየተሰጠ እንዳልሆነ ተገልጿል፡፡ ችግሩን ለሚዲያ እንዳይነገርም የወረዳና በመቀሌ ያሉ የሕወሓት ባለሥልጣናት ለመከላከል ጥረት እያደረጉ ስለመሆኑም ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ሰዓት በትግራይ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ተፈናቃዮች አሉ፡፡ በረሃብ ተጋልጠው ያሉት ተፈናቃዮች ብቻ ሳይሆኑ በቀዬአቸው ላይ ያሉትም ናቸው፡፡ ‹‹በጦርነቱ ወቅት አካባቢያችን በኤርትራ ወታደሮች ተወሮ ነበር፡፡ ሰብል አወደሙ፡፡ ምንም ንብረት አላስቀሩም፡፡ ለማረስ በሬ የለም፡፡ ዕርዳታም ከተቋረጠብን አምስት ወራት አለፈው፤›› ስትል በሳምር ወረዳ የደብረ ኃይለ ከተማ ነዋሪ ለሪፖርተር የተናገረችው የአምስት ልጆች እናት ስትሆን ባሏ በጦርነቱ ቆስሎ ሆስፒታል እንደሚገኝ ገልጻለች፡፡  

በትግራይ በተለያዩ ከተሞች ዙሪያ ያሉት ተፈናቃዮችም ከሰሜንና ምዕራብ ትግራይ የተፈናቀሉ ሲሆን፣ ወደቀዬአቸው እንዳይመለሱ ችግር እንደገጠማቸው ተናግረዋል፡፡

‹‹ሁላችንም ከሁመራና ወልቃይት ነው የተባረርነው፡፡ እዚህ ቁጭ ብለን ዕርዳታም ምንም የለም፡፡ መንግሥት ሰላም ነው ካለ መሬታችንን ካስለቀቀልን ወደ ቀዬአችን ተመልሰን አርሰን መብላት ነው የምንፈልገው፤›› ሲሉ አቶ ታደሰ ይልማ ገልጸዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የቤት ባለንብረቶች የሚከፍሉትን ዓመታዊ የንብረት ታክስ የሚተምን ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጀ

በአዋጁ መሥፈርት መሠረት የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የንብረት ታክስ መጠን...

እንደ ንብረት ታክስ ያሉ ወጪን የሚያስከትሉ አዋጆች ከማኅበረሰብ ጋር ምክክርን ይሻሉ!

የመንግሥትን ገቢ በማሳደግ ረገድ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የሚታመኑት የተጨማሪ እሴት...

ለዓለምም ለኢትዮጵያም ሰላም እንታገል

በበቀለ ሹሜ ያለፉት ሁለት የዓለም ጦርነቶች በአያሌው የኃያል ነን ባይ...