የቀድሞ የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን፣ የቅዱስ ጊዮርጊስ ወጣትና ሴቶች ቡድን አሠልጣኝ የነበረችው ሰላም ዘርዓይ የላይቤሪያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለማሠልጠን መስማማቷ ተገለጸ፡፡
ላይቤሪያ የብሔራዊ ቡድን አሠልጣኙን ማሰናበቱንና አሠልጣኝ ለመቅጠር ማስታወቂያ ማውጣቱን ተከትሎ፣ አምስት ወራት በፈጀው የቅጥር ሒደት ያለፈችው ኢትዮጵያዊቷ አሠልጣኝ ለመሾም ከስምምንት መድረሷ ተጠቅሷል፡፡
በሒደት ላይ መሆኗ ለሪፖርተር የገለጸችው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ኢንስትራክተሯ ሰላም፣ የላይቤሪያን የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለማሠልጠን ፊርማዋን ስታኖር፣ በተጨማሪ ከ17 ዓመት በታችና ከ20 ዓመት በታች ጭምር እንደምታሠለጥን ተገልጿል፡፡
የካፍ ኢንስትራክተሯ ሰላም የኢትዮጵያ ታዳጊ ቡድን እንዲሁም በዘንድሮ የውድድር ዓመት የአቃቂ ቃሊቲ የሴቶች ቡድን ስታሠለጥን መቆየቷ ይታወሳል፡፡
ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያዊት አሠልጣኝ ወደ ውጭ አገሮች አምርታ ብሔራዊ ቡድኖች የማሠልጠን ልምድ የሌለ ሲሆን በአንፃሩ፣ ወንድ አሠልጣኞች በሱዳንና የመን የማሠልጠን ልምድ እንዳላቸው ይታወቃል፡፡
ከዚያም ባሻገር የካፍ ኢንስትራክተርነት ማዕረግ ያላቸው ኢትዮጵያውያን የእግር ኳስ ባለሙያዎች ልምዳቸውን ለተለያዩ የአፍሪካ አገሮች ጀማሪ አሠልጣኞች ትምህርት ሲሰጡ ይስተዋላል፡፡ የላይቤሪያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በቅርቡ የኢትዮጵያዊቷን ቅጥር ይፋ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡