‹‹ኢትዮጵያ መጠነ ሰፊ የሆነ የታሪክ፣ የተፈጥሮና የባህል ውብ እሴቶችን በስብጥር አቅፋና ደግፋ ለብዙ ዓመታት የኖረች እንዲሁም የተሻገረች አገር ነች፤›› የሚለው የኢትዮጵያ ቱሪስት አስጎብኚ ባለሙያዎች ማኅበር (ኢቱአባማ) ነው።
ኢቱባአማ ይህንን ስብጥር የሚያጎላ በኢትዮጵያ ቱሪዝም ፀጋዎችና ውብ እሴቶች ላይ የሚያተኩር፣ ‹‹ኢትዮጵያ በቱሪስት አስጎብኚዎቿ ዕይታ ኢትዮጵያን ለትውልድ›› የተሰኘ ሁለተኛውን ዓውደ ርዕይ ከግንቦት 29 ቀን 2015 ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ አበባ ሙዚየም ለሳምንት ያህል እያሳየ ነው።
ዓውደ ርዕዩ በዋናነት ለኢትዮጵያ የማይመጥነውን አሉታዊ ገጽታ ከመቀየር አንፃር የራሱን አሻራ ያኖራል ተብሎ የታሰበ መሆኑን የገለጸው ማኅበሩ፣ ኅብረተሰቡ የውሎ ቀጠሮውን በአዲስ አበባ ሙዚየም ይሆን ዘንድ ጥሪውን አስተላልፏል።
ከዓውደ ርዕዩ ጎን ለጎንም ‹የቱሪስት አስጎብኚ ባለሙያነት በኢትዮጵያ› በሚል ርዕስ ውይይት አካሂዷል።
ከታሪካዊ የጉዞ መስመር ከአክሱም ላሊበላ፣ ከጎንደር እስከ ሐረር፣ ከስሜን ተራሮች እስከ ባሌ ተራሮች፣ ከአዋሽ ሸለቆ እስከ ኦሞ ሸለቆ እንዲሁም በሌሎች ባህላዊና ሃይማኖታዊ ቅርሶችን ጭምር ለውጭ አገርም ሆነ ለአገር ውስጥ ቱሪስቶች በማስጎብኘት፣ በማብራራት ከሚሠለፉት በቀዳሚነት የሚጠቀሱት አስጎብኚ ባለሙያዎች ማኅበራቸውን የመሠረቱት ከሦስት ዓመት በፊት ሰኔ 12 ቀን 2012 ዓ.ም. ነው፡፡