በትግራይ የሰላም ስምምነት ተግባራዊ በሚደረግበት ወቅት የዘር ማፅዳት እየተካሄደ ነው ሲል ሒዩማን ራይትስዎች ግንቦት 24 ቀን 2015 ዓ.ም. ያወጣው ሪፖርት፣ አገሪቱ እያደረገች ያለውን የዕርቅና የምክክር ሒደት የሚያደናቅፍ መሆኑን መንግሥት አስታወቀ፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ማክሰኞ ግንቦት 29 ቀን 2015 ዓ.ም. በሰጠው ምላሽ፣ ‹‹በሰሜኑ የአገራችን ክፍል የነበረው ግጭት በርካታ አካባቢዎችን ለጉዳት ያጋለጠ ቢሆንም፣ በተለየ ሁኔታ የተወሰነ አካባቢን መርጦ ደጋግሞ ሪፖርት በማዘጋጀት፣ በሰብዓዊ መብት አጀንዳ ሽፋን የተለየ የፖለቲካ ተልዕኮን ለማሳካት ዓላማ ያደረገ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፤›› ብሏል፡፡
ሒዩማን ራይትስዎች የአማራ ኃይሎችና የአካባቢው ባለሥልጣናት በጉልበት የትግራይ ተወላጆችን ማፈናቀላቸውን መቀጣላቸውን፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ይህንን ድርጊት በመፈጸም ላይ የሚገኙ የፀጥታ ኃይሎችን እንዲያግድ፣ እንዲመረመርና በአግባቡ እንዲቀጣ ሲል መጠየቁ ይታወሳል፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት በበኩሉ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የነበረው ግጭት በርካታ አካባቢዎችን ለጉዳት ያጋለጠ ቢሆንም፣ ሒዩማን ራይትስዎች በልዩ ሁኔታ የተወሰነ አካባቢን መርጦ ደጋግሞ ሪፖርት በማዘጋጀት፣ በሰብዓዊ መብት አጀንዳ ሽፋን የተለየ የፖለቲካ ተልዕኮውን ለማሳካት ዓላማ ያደረገ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም ብሏል፡፡ የቀረበው ሪፖርት ይዘት ሲታይም ተገቢው ምርመራ ያልተደረገበት፣ በበቂ ማስረጃ ያልተደገፈና እምነት የሚጣልበት አይደለም ሲል አጣጥሎታል፡፡
በሒዩማን ራይትስዎች የቀረበው ሪፖርት የተዛባና በአካባቢው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የማይገልጽ፣ ለዘመናት አብረው የቆዩ ሕዝቦችን አብሮ የመኖር እሴት የሚያጠለሽ፣ በሕዝቦች መካከል ግጭት ቀስቃሽ የሆነና አገሪቱ እያደረገች ያለውን የዕርቅና የምክክር ሒደት የሚያደናቅፍ አሉታዊ ተፅዕኖ ያለው ሪፖርት ሆኖ ማግኘቱን አስታውቋል።
መንግሥት በሰሜን ኢትዮጵያ በነበረው ግጭት ተፈጸሙ የተባሉ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ጽሕፈት ቤት ጥምር የምርመራ ቡድን እንዲያጣሩ አስፈላጊውን ሁኔታ በማመቻቸት፣ ሪፖርቱም ሲወጣም የተሰጡ ምክረ ሐሳቦችን ለመተግበር የሚኒስትሮች ጥምር ግብረ ኃይል በማቋቋም መጠነ ሰፊ የሆኑ ተጎጂዎችን መልሶ የማቋቋም፣ ተፈጸሙ የተባሉ የመብቶች ጥሰቶች ምርመራና የሕግ ማሻሻያ ሥራዎችን ሲሠራ መቆየቱ በመግለጫው ተዳሷል።
በተጨማሪም በፕሪቶሪያ የተደረሰውን የሰላም ስምምነት ለማስፈጸም፣ እንዲሁም በአገሪቱ የሚታዩ አለመግባባቶችን በዘላቂነት ለመፍታት የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አማራጮች ተዘጋጅተው በአገር አቀፍ ደረጃ በርካታ ውይይቶች እየተደረጉ እንደሚገኙ ያስታወቀው የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት፣ በቀረቡ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አማራጮች ላይ ከመንግሥታዊ ተቋማት፣ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ተወካዮችና ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አባላት ጋር ሰፊ ምክክሮችና የግብዓት ማሰባሰቢያ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጿል፡፡
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት መግለጫውን ሲያጠቃልልም መንግሥት በአገሪቱ ያሉ ችግሮችን ከመሠረቱ ለመቅረፍ ከሚሠራቸው ሥራዎች በተጨማሪ፣ ኢሰመኮና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር ጽሕፈት ቤት ጥምር የክትትል ቡድን ተደራጅቶ፣ ግጭቱ በነበረባቸው አካባቢዎች ያለውን የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል እንዲያደርጉ በመጋበዝ በኃላፊነት መንፈስ እየሠራ ባለበት ወቅት፣ ሒዩማን ራይትስዎች ጉዳዩን ከግንዛቤ ሳያስገባና በቂ ማስረጃ በሌለበት ያወጣው ሪፖርት ገንቢ ያልሆነና ፈጽሞ ተቀባይነት የለውም ብሏል።