የዓለም ምግብ ፕሮግራምና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ተራድዖ ድርጅት በትግራይ ሲያከናውኑ የነበረውን የምግብ ዕርዳታ፣ ከአንድ ወር በፊት ማቋረጣቸውን ተከትሎ፣ ዕርዳታው በድጋሚ በሚጀምርበት ሁኔታ ላይ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደርና የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛን ከያዘ ልዑክ ጋር መወያየታቸው ተገለጸ፡፡
በተራድዖ ድርጅቶቹ የሚሰጡት የምግብ ዕርዳታ ለሌላ ዓላማ እየዋሉ እንደሆነ በመግለጽ፣ ዕርዳታቸውን በትግራይ ክልል አቁመው የድርጅቶቹ ከፍተኛ ኃላፊዎችና አሜሪካን ጨምሮ የአገሮች መንግሥታት በድርጊቱ ላይ ምርመራ እንዲያካሄድ ሲጠይቁ እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡
የአሜሪካ የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ማይክ ሐመር (አምባሳደር)፣ ባለፈው ሳምንት ጀምሮ በጂቡቲ ጉብኝት ያካሄዱ ሲሆን፣ በኢትዮጵያም በትናንትናው ዕለት ግንቦት 28 ቀን 2015 ዓ.ም. ከትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ ጋር መወያየታቸው ተገልጿል፡፡
አቶ ጌታቸው በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው እንደገለጹት ሐመር (አምባሳደር) እና የአሜሪካ ኤምባሲ በኢትዮጵያ ጉዳይ ፍፃሚ ትሬሲ ጃኮብሰን መቀሌን ሲጎበኙ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ገለጻ አድርገውላቸዋል፡፡
አቶ ጌታቸው እንዳጋሩት መረጃ አንደኛው ገለጻ ያደረጉላቸው ጉዳይ የምግብ ዕርዳታውን ለማቆሙ ምክንያት የሆነው፣ ለታመለት ዓላማ ያለመዋሉን በሚመለከት ጊዜያዊ አስተዳደር ምርመራ እያደረገ እንደሆነና በተደረገው ምርመራ ያገኙትን ውጤቶችም ለልዑክ ቡድኑ ማጋራታቸውን አሳውቀዋል፡፡
‹‹ግኝቱን ለሕዝብ ይፋ እንደምናደርግና በቅርቡም እጃቸው ያለበትን ተጠያቂ እንደምናደርግ አረጋግጠንላቸዋል፤›› ብለው የገለጹት አቶ ጌታቸው፣ አሜሪካ ዕርዳታውን ለክልሉ ሕዝቦች ማድረሷን መልሳ እንድትጀምርም ጥያቄ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡
በዚህ ሳምንት ሰኞና ማክሰኞ ግንቦት 28 እና 29 ቀን 2015 ዓ.ም. ከጂቡቲ መልስ በኢትዮጵያ ጉብኝት ያደረጉት አምባሳደር ማይክ፣ ከትግራይ ጊዜያዊ አስተተዳደር በተጨማሪም፣ በመቀሌ በሚገኝ የተፈናቃዮች መጠለያ ጣቢያ ጉብኝት ማድረጋቸው ታውቋል፡፡
በተጨማሪም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳሳወቀው፣ ልዩ መልዕክተኛው ከሚኒስትር ደኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ ጋር ማክሰኞ ግንቦት 29 ቀን 2015 ዓ.ም. ተገናኝተው ‹‹የሁለቱ አገሮች ግንኙትን በማጠናከር ላይ ያተኮረ›› ውይይት አድርገዋል፡፡
የዓለም ምግብ ፕሮግራም የኢትዮጵያ ቢሮ የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊዋ ክሌር ኔቪል ለሪፖርተር በላኩት መልዕክት፣ ለዕርዳታ የተላከው ምግብ በገበያ እየተሸጠ መሆኑን ማስረጃ በማግኘቱ ተቋሙ ድጋፍ ማድረጉን ማቆሙን ተናግረው፣ የሕይወት አድን የሆኑ ምግቦች ለሚያስፈልጋቸው ዜጎች እንዳይዳረስ የሚያደረግን እክል ለማስቆም አጠናክረው እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡
‹‹ሕይወት አድን ምግብ ዕርዳታው ከዚህ በኋላ እንቅፋት እንዳይገጥመው ሁሉን አቀፍና ጥበብ የተሞላበት አሠራር እየዘረጋን ነው፤›› ብለው የገለጹት የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊዋ፣ የተቋሙ ሠራተኞች በቦታው በመገኘት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ድጋፍ መልሶ በሚጀምርበት ዙሪያ ላይ በቅርበት እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የተቋሙ በኢትዮጵያ ዋና ዳይሬክተር ካላውዴ ጂቢዳርና ምክትላቸው ጄኔፈር ቢቶንዴ፣ በትግራይ የምግብ ዕርዳታ ከመቋረጡ ጋር በተያያዘ ከሥራቸው በፈቃዳቸው ለቀዋል ተብሎ በተለያዩ የሚዲያ ተቋማት ሲዘገብ የቆየ ሲሆን፣ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የኮሙዩኒኬሽን ኃላፊዋ ግን፣ ይህ እውነት እንዳልሆነና በተቋሙ ምንም ዓይነት የከፍተኛ አመራር ሥራ መልቀቅ እንዳልተካሄደ ተናግረዋል፡፡
‹‹ዳይሬክተሩ ክላውዴ ዕረፍት ላይ ሲሆኑ፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ሠራተኝነታቸውም ይቀጥላል፡፡ ጄኔፈርን ጨምሮ ሁለቱም ምክትል ኃላፊዎች በቦታቸው ነው ያሉት፤›› ብለው የገለጹት ክሌር፣ ለተቋሙ ምንም ዓይነት የሥራ መልቀቅ ማመልከቻ እንዳልገባ በመግለጽ፣ ማከሰኞ ግንቦት 29 ቀን 2015 ዓ.ም. ለሪፖርተር መልዕክት ልከዋል፡፡