በአበበ ፍቅር
በደቡብ አፍሪካ ስዌቶ ከተማ እ.ኤ.አ. በ1976 በወቅቱ የነበረውን የአፓርታይድ ሥርዓት ተቃውመው የወጡ ሕፃናት ላይ ከፍተኛ የሆነ ጭፍጨፋ ደርሶባቸው ነበር፡፡
ሕፃናቱ ለተቃውሞ የወጡትም ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት በቋንቋቸው እንዲሰጣቸውና እንዲማሩ ለመጠየቅ ነበር፡፡
በተቃውሞው የተሳተፉት 20 ሺሕ ያህል ተማሪዎች ሲሆኑ፣ ፖሊሲ በወሰደው ዕርምጃ 250 ተማሪዎች የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ መቶ የሚደርሱ ተማሪዎች እንደሞቱም ናሽናል ቱዴይ በድረ ገጹ አስፍሯል፡፡
ይህንን አስከፊ ክስተት ለማስታወስ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እ.ኤ.አ. ከ1991 ጀምሮ በየዓመቱ ሰኔ 9 ቀን ‹‹የአፍሪካ ሕፃናት ቀን›› በሚል ታስቦ እንዲውል ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ቀኑ በየዓመቱ ይከበራል፡፡
ሰኔ 9 ቀን 2015 ዓ.ም. የሚከበረው የአፍሪካ ሕፃናት ቀን አስመልክቶም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሴቶች፣ ሕፃናትና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ዝግጅት ማድረጉን አስታውቋል፡፡
ዕለቱ ‹‹ሰላም፣ ፍቅር፣ እንክብካቤና ጥበቃ ለሁሉም ሕፃናት›› በሚል መሪ ቃል በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚከበር በቢሮው የሕፃናት ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ ሕይወት ጉግሳ ተናግረዋል፡፡ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕፃናት ቀን ዓላማ ማኅበረሰቡ በሕፃናት ላይ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችንና ጥቃቶችን በመገንዘብ ለሕፃናት ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ እንዲያደርግ ግንዛቤ ለመፍጠርና ሕፃናትን ያሳተፈ ንቅናቄ ለማድረግ ሲሉ ኃላፊዋ አክለዋል፡፡
ከልጅ አያያዝ፣ አስተዳደግ ግንዛቤና ዕውቀት ማነስ ከሉላዊነት የቴክኖሎጂ ዕድገት፣ ከሕዝብ ቁጥር መጨመር፣ መጤ ባህሎችና ሌሎችም ልዩ ልዩ ምክንያቶች ጋር በተያያዘ በሕፃናት ላይ የሚፈጸሙ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እየተስፋፉና መልካቸውን እየቀያየሩ መምጣታቸውን የተናገሩት ወ/ሮ ሕይወት፣ ይህንን በመገንዘብ ሕፃናትን ከልዩ ልዩ ጥቃት መከላከልና ጥበቃ ሊደረግላቸው ይገባል ብለዋል፡፡
ከሕፃናቱ ጋር ተያይዘው የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመቀነስ ተቋሙ በሕፃናት ሁለንተናዊ መብት መጠበቅ፣ ከለላና ጥበቃ ዙሪያ ለ350 ሺሕ በላይ የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራን መሥራቱን ተናግረዋል፡፡
በዚህም ለ25 ሺሕ ሕፃናት የልደት ምዝገባ፣ በሕግ አባትን የማወቅ፣ ጥቃት የደረሰባቸውና ሕግ ተላልፈው ለተገኙ ተሃድሶ እንዲያገኙ መደረጉን ኃላፊዋ አክለዋል፡፡
ሕፃናትንና አረጋውያንን ከጎዳና በማንሳት ሒደት ደኅንነታቸው ባልተጠበቀ አካባቢ በማሰባሰብ ለተለያዩ ጉዳቶች ተጋላጭ ሆነዋል ተብሎ ለሚቀርበው አቤቱታ የቢሮው የማኅበራዊ ዘርፍ ኃላፊ ወ/ሮ ገነት ቅጣው እንዳሉት፣ ቃሊቲ የሚገኘው የአረጋውያን ማገገሚያ ተቋም፣ ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ተጋላጭ የነበሩ ሕፃናት አረጋውያንና ሴቶችን በመንግሥት በጀት በማሰባሰብና ሙሉ እንክብካቤ በመስጠት እስከ ዘላቂ ማረፊያ አገልግሎት ሲሰጥበት ቆይቷል፡፡
ተቋሙ ሲሰጥ የነበረውን አገልግሎት ከሰባት ወር በፊት በማቋረጥ ለተሻለ አገልግሎት እየተዘጋጀ ሲሆን፣ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋላም ለተለያዩ ማኅበራዊ ችግሮች ለተጋለጡ በተለይ ደግሞ በወሲብ ንግድ ላይ ለተሰማሩ ሴቶች ማገገሚያና ማቋቋሚያ ለማድረግ መታሰቡን አክለዋል፡፡
በመጀመርያ ዙር ውሎ አዳራቸውን በጎዳና ያደረጉ ሰባት ሺሕ፣ በሁለተኛው ዙር 97 እንዲሁም በሦስተኛ ዙር 246 ሕፃናትን ማንሳታቸውን ገልጸዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ 1,777 ሕፃናትን ማንሳታቸውን፣ ከዚህ በተጨማሪ ከ69 ሺሕ በላይ ሕፃናትን ወደ ቤተሰባቸው መልሶ ማቀላቀልና የማቋቋም ሥራ መከናወኑን እንዲሁም በአማራጭ የድጋፍ ክብካቤ አገልግሎት ተጠቃሚ እንደሆኑ መደረጉን ኃላፊዋ ገልጸዋል፡፡
በ2015 በጀት ዓመት 790 ሕፃናት በአገር ውስጥ ጉዲፈቻና 35 ሕፃናት ደግሞ በአደራ ቤተሰብ አገልግሎት ተጠቃሚ እንደሆኑ መደረጉን፣ በአጠቃላይ ከ2009 ዓ.ም. ጀምሮ 1,365 የሚሆኑ ዜጎቹ ከጎዳና ላይ መነሳታቸውን አብራርተዋል፡፡
የሕፃናት ውክልናና ተሳትፏቸውን ከማረጋገጥ አንፃር 5,206 ሕፃናት በበጎ ፈቃድ ተግባራት፣ በኩነቶችና በሕፃናት ፓርላማ ተሳትፈዋል ብለዋል፡፡
ጉዳት የደረሰባቸው 755 ሕፃናት በጋንዲ፣ በጥሩነሽ ቤጂንግ፣ በዳግማዊ ምኒልክና በአበበች ጎበና ሆስፒታሎች ሆነው የሕክምናና የሥነ ልቦና ማኅበራዊ ድጋፍ ዕገዛ እንዲያገኙ ተደርጓል ሲሉ ኃላፊዋ ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል በመንግሥት ሴክተር መሥሪያ ቤቶች 54 የሕፃናት የቀን ማቆያዎች መኖራቸውን፣ በዚህም 710 ሕፃናት ተጠቃሚ መሆናቸውን አክለዋል፡፡