ምክኑስ? አልኩ፡፡
ነገሩ የምፀት ነው፡፡
ብዙ አስቤ ተመራምሬ፣
በዚህ የእኔ – ዐዋቂነት ላይ አትኩሬ፣
ራሴን ከፍ አድርጌ አክብሬ፣
በለቀምኩት፣ ባካበትኩት ጥሬ ዕውቀት
ብዙ ኮርቼ፤
ከኩራቴም ብዛት፣ ብ–ዙ፣ እጅጉን ብ–ዙ ታብቼ፣
እጅጉን ብ-ዙ ቆይቼ፣
ድንገት – እንዴው ድንገት
ጎዶሎ አንደበቴ ብትፈታ አንድ ጥያቄ ተጠይቄ፤
‹‹ቡና ይምጣልዎ ማኪያቶ?››
የምትል፤
‹‹ለማንኛውም እስቲ ጉዳዩ ይቅረብልኝ
‹‹በመጀመሪያ ተጠንቶ፡፡››
ብዬ ተነፈስኩኝ፤ ጥናት ልምድ ሆኖብኝ፡፡
እናም፣ ሊጠጣ የቀረበ ቡና፤ እናም ማኪያቶ፤
እንዲመለስ ሆነ፤ ዳግም እንደገና ሊቀርብ ተጠንቶ፡፡
ሲጠና፤
ሁሉም በረደና፤
በሪዱ ቆይቶ ቀረበና፤ በመብረዱም ተናቀና፤
ሊጠና የሄደው ማኪያቶ፣ ደግሞም ቡና፤
ተጎልቶ ከዚያው ቀረ፤ እንዳልነበረ ተረሳና፤
ደግሞ እስኪፈላ ሌላ ቡና፡፡
መጋቢት 1966 ዓ.ም.
- ዮናስ አድማሱ ‹‹ጉራማይሌ›› (2006 ዓ.ም.)