የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከአራት ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የመሬት ሊዝ ጨረታ አወጣ ። ለጨረታ የቀረቡት ይዞታዎች መነሻ ዋጋ ከፍተኛው 2,213 ብር መሆኑ ታውቋል።
የአዲሰ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ዛሬ ግንቦት 7 ቀን 2015 ዓም ይፋ እንዳደረገው፣ በከተማዋ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች 297 ይዞታዎችን ለተጠቃሚዎች በሊዝ ለማስተላለፍ ጨረታ ውጥቷል።
በሊዝ ጨረታ እንዲተላለፉ የተዘጋጁት 297 ይዞታዎች አጠቃላይ ካሬ ሜትር 143 ሺህ (14 ነጥብ 3 ሄክታር) ሲሆኑ፣ ይዞታዎቹ በአስራ አንዱም ክፍለ ከተሞች የሚገኙ ናቸው ብሏል።
ለጨረታ ከሚቀርቡ ቦታዎች መካከልም ከዚህ ቀደም በምደባና በጨረታ ወስደው ያላለሙና እርምጃ የተወሰዳባቸው፣ በተለያዩ ጊዜያት በህገ ወጥ መንገድ የተወረሩና ወደ መሬት ባንክ የገቡ መሬቶች እንደሚገኙበት አስታውቋል።
ለጨረታ የቀረቡት ይዞታዎች ዝቅተኛው የጨረታ መነሻ ዋጋ በካሬ ሜትር 960.21ብር ሲሆን፣ ከፍተኛ የተባለው መነሻ ዋጋ 2,213. 25 ብር መሆኑን ቢሮው አስታውቋል።
በጨረታው መሳተፍ የሚፈልጉ ከግንቦት 10 ቀን 2015 ዓ.ም እስከ ከግንቦት 23 ቀን 2015 ዓ.ም ከቀኑ 9 ሰዓት ድረስ ለም ሆቴል አካባቢ በሚገኘው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ በመገኘት የጨረታ ሰነዱን ገዝተው መሳተፍ እንደሚችሉ ገልጿል።
ተጫራቾች ለሚወዳደሩበት ይዞታ የተቀመጠውን መነሻ ዋጋ መሠረት በማድረግ ከአጠቃላይ ዋጋው 20 በመቶውን ለጨረታ ማስከበሪያ ዋስትና በባንክ የክፍያ ማዘዣ /ሲፒኦ/ ማስያዝ እንደሚጠበቅባቸው ገልጿል።
በዚህ ጨረታ ኢትዮጵያዊ የሆኑ ግለሰቦች ፣ የንግድ ማኅበራት ፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያን እንዲሁም በአንድ የጨረታ ሰነድ ከአንድ ሰው በላይ ሆኖ መወዳደር እንደሚቻል አመልክቷል።
ጨረታው ተጫራቾች ወይም ህጋዊ ወኪሎቻቸው በተገኙበት ግንቦት 24 ቀን 2015 ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡ዐዐ ሰዓት ጀምሮ በ5 ተከታታይ የስራ ቀናት በቦሌ ክፍለ ከተማ አዳራሽ እንደሚከፈት አስታወቋል።