የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የአዲስ አበባ ብሔራዊ ስታዲየም ችግር እንዲፈታ በተደጋጋሚ ቢያሳስብም ችግሩን ሊፈታ አለመቻሉን አስታውቋል፡፡
ሚያዝያ 24 ቀን 2015 ዓ.ም. የባህልና ስፖርት ሚኒስቴርና የተጠሪ ተቋማትን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ያዳመጠው ቋሚ ኮሚቴው፣ ሚኒስቴሩ በስታዲየሞች ላይ የሚስተዋሉ መጓተቶችን ሊፈታ እንደሚገባ አሳስቧል፡፡
ቋሚ ኮሚቴው በአዲስ አበባ ከተማ ባደረገው የመስክ ምልከታ ወቅት፣ የአዲስ አበባ ስታዲየም ዕድሳት ተደርጎለት፣ በመጋቢት ወር 2015 ዓ.ም. በከተማዋ ለሚካሄደው ዓለም አቀፍ ውድድር ይደርሳል ቢባልም፣ ግንባታው ባለመጠናቀቁ ማስተናገድ እንዳልተቻለ ተጠቅሷል፡፡
ከዚህም ባሻገር ሁለተኛውን ዙር ለማደስ ቀደም ሲል የተገባው ውል ተቋርጦ ከአዲስ ኮንትራክተር ጋር ውል የተገባበት ምክንያት በግልጽ አለመታወቁንም ቋሚ ኮሚቴው አንስቷል፡፡
ይህም ዕድሳቱ በተያዘለት ጊዜ ባለመጠናቀቁ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአገር ውጭ ያለ ተመልካች እንዲጫወት መገደዱንና ለከፍተኛ ወጪ መዳረጉን በቋሚ ኮሚቴ ተጠቅሷል፡፡
የባህልና ስፖርት ሚኒስትር አቶ ቀጀላ መርዳሳ በበኩላቸው፣ የስታዲየሙ ችግር ውስብስብ በመሆኑና የዕድሳት ሥራውን ለመጨረስ የተመደበው ገንዘብ አነስተኛ መሆኑን አስረድተው፣ ችግሩን ለመፍታት የበርካታ ባለድርሻ አካላትን ርብርብ ይጠይቃል ብለዋል፡፡
‹‹የስታዲየም ዕድሳቱን ለማከናወን ከገንዘብ እጥረት ባለፈም ወቅቱ ዝናባማ በመሆኑ ዕድሳቱን ሊያጓትተው ችሏል፡፡ ያጋጠመውን ችግር ለመፍታት ሚኒስቴሩ በከፍተኛ ኃላፊነት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፤›› በማለት አቶ ቀጀላ ተናግረዋል።
ቀደም ሲል ውል ይዞ ሲገነባ የነበረው ኮንትራክተር ውል ተቋርጦ ከአዲስ ኮንትራክተር ጋር ውል የተገባበት ምክንያት ምንድነው? የሚል ጥያቄ የተነሳ ሲሆን፣ ቀደም ሲል ከነበረው ኮንትራክተር ጋር የተቋረጠ ውል አለመኖሩን ገልጸው፣ ኮንትራክተሩ ውሉን ጨርሶ በመውጣቱ ተገልጿል፡፡
ሚኒስቴሩ የአዲስ አበባ ስታዲየምን ችግር እንዲፈታ ቋሚ ኮሚቴው በተደጋጋሚ ቢያሳስብም ችግሩን ሊፈታ ስላልቻለ፣ ችግሩን ለአፈ ጉባዔው በጽሑፍ እንዲቀርብ ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል የወጣቶች ስፖርት ማዘውተሪያ ችግር አለመፈታቱ፣ ተተኪ ስፖርተኞችን ከማፍራት አኳያ ውስንነት መኖሩ፣ ስፖርትን ከማልማት አኳያ ሕዝባዊ ለማድረግ በቂ ሥራ አለመሠራቱንና ከፌዴሬሽኖች ጋር ያለውን ክፍተት ለመፍታት መቀራረብ እንደሚገባ ተነስቷል፡፡