ያለ ፕሬስ ነፃነት ዴሞክራሲን ማምጣት ወይም ማረጋገጥ የማይታሰብ ጉዳይ መሆኑን የገለጹ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች፣ መንግሥት በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጠውን የፕሬስ ነፃነት እንዲያከብርና ትኩረት እንዲሰጥ ጠየቁ፡፡
ለረዥም ዓመታት የፕሬስ ነፃነት ካልተረጋገጠባቸው አገሮች ተርታ ደግሞ ኢትዮጵያ ስሟ ቀድሞ ይነሰ እንደነበር ያስታወሱ ባለሙያዎቹ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የሚመራው መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ፣ ለአንድ ዓመት ያህል ለውጥ ያሳየው የኘሬስ ነፃነት ወደ ቀድሞ ሥጋቱ እየተመለሰ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በየዓመቱ የአገሮችን የፕሬስ ነፃነት ደረጃ እየመዘነ የሚሰፍረው ዓለም አቀፉ ድንበር የለሽ የጋዜጠኞች ቡድን፣ ኢትዮጵያ ቀድሞ ከነበሩ ዓመታት አንፃር ሲታይ ደረጃዋን አሻሽላ እንደነበር ጠቅሷል። ሆኖም ባለፉት ሦስት ዓመታት የአገሪቱ ደረጃ ዝቅ ብሏል።
ዘንድሮ ለ30ኛ ጊዜ የተከበረው የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን ‹‹የወደፊቱን መብቶች መቅረፅ›› በሚል መሪ ሐሳብ ታስቦ ውሏል።
በኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት፣ በዩኔስኮና በካርድ ትብብር በኢንተር ሌግዤሪ ሆቴል እ.ኤ.አ ሜይ 3 ቀን 2023 በተከበረው የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ጋዜጠኞችና ምሁራን ተገኝተዋል። በዕለቱም የፓናል ውይይት ተካሂዷል። ውይይቱ ታሳታፊ የነበሩት በአዲስ አባባ ዩኒቨርሰቲ የጋዜጠኝነትና ሥነ ተግባባት ትምህርት ቤት ሙላት ዓለማየሁ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በፕሬስ ነፃነት ከዓለም አገሮች ደረጃዋ እያሽቆለቆለ መምጣቱን ተናግረዋል።
እ.ኤ.አ የዘመን ቀመር በ2019 ቀን 140ኛ የነበረችው ወደ 110ኛ፣ 2020 ደግሞ 100ኛ ከዚያም 99ኛ ደረጀን በመያዝ የተሻለ ውጤት አስመዝግባ እንደነበር አውስተው፣ ባለፈው ዓመት ወደ 114ኛ ዝቅ ማለቷን አስረድተዋል። በዘንድሮ ዓመት ደግሞ ከ180 አገሮች 130ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ብለዋል።
እንደ ረዳት ፕሮፌሰር ሙላት ዓለማየሁ ገለጻ ይህ የሚያሳየው በአገሪቱ ምን ያህል የፕሬስ ነፃነት እየቀነሰ መምጣቱን ነው።
በዕለቱ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ሊቀመንበር አቶ አማረ አረጋዊ መንግሥት የመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ሕግና ድንጋጌዎችን ተግባራዊ በማድረግ ሕገ መንግሥታዊ ግዴታውን እንዲወጣ ጠይቀዋል።
በተለይ የሚዲያ ባለሙያዎች በሕግ ተጠያቂ ሲሆኑ የመገናኛ ብዙኃን አዋጁ ተግባራዊ ሊሆን እንደሚገባ አስረድተዋል። ደራሲና ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ጋዜጠኞች በተለይ በዚህ ወቅት ከፍተኛ የደኅንነነት ሥጋት ውስጥ ገብተዋል ብለዋል።
ጋዜጠኞችም ድምፅ ለሌላቸው ድምፅ በመሆን ሙያዊ ሥነ ምግባርን አክብረው እንዲሠሩ ጠይቀዋል።
የዩኔስኮ ተወካይ አብዱላሂ ሳሊፎ (ዶ/ር) የፕሬስ ነፃነት ቀን በመላው ዓለም የሚከበር መሆኑን አውስተው፣ በብዙ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፈው ለሚሠሩ ባለሙያዎች ዕውቅና መስጠት እንደሚገባ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር)፣ የአገራችን ፕሬስ ነፃነት ጥያቄ ውስጥ ገብቷል ብለዋል።
በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት በሚዲያና በሚዲያ ሠራተኞች ላይ እየጨመረ የመጣው እንግልት፣ ማዋከብና እስር እጀግ አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል።
በተለይ በጋዜጠኞች ላይ የሚፈጸመው እስር ሕግና ድንጋጌዎችን ሊከተል ይገባዋል ብለዋል።
የዘንድሮው የፕሬስ ነፃነት ቀን በኢትዮጵያ በፓናል ውይይትና በተለያዩ ሁነቶች ተከብሮ ውሏል።
በፓናል ውይይቱ ተሳታፊ የነበሩ ጋዜጠኞችም በተለይ በአሁኑ ወቅት ለዘገባ በነፃነት መንቀሳቀስ እንዳልቻሉ ተናግረዋል።
‹‹በየኬላው የጋዜጠኛ መታወቂያ ስናሳይ ለእንግልትና መጉላላት እንዳረጋለን›› ሲሉ ቅሬታቸውን ተናግረዋል።
ይህም ሙያዊ ክብርን የሚጋፋ በመሆኑ መንግሥት ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጠው ጠይቀዋል።