በኮሌራ ወረርሽኝ የሚጠቁ ሰዎች ቁጥር በየወሩ እየጨመረ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ ለሪፖርተር ገለጸ፡፡ ወረርሽኙ ከተከሰተ ከስምንት ወራት በላይ እንዳስቆረ፣ በወረርሽኙ የሚጠቁ ሰዎች ቁጥር በየቀኑ እየጨመረ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ ድንገተኛ የኅብረተሰብ ጤና ቁጥጥርና ምርምር ዳይሬክተር አቶ ገመቹ ሹሜ ተናግረዋል፡፡
‹‹ከወር እስከ ወር ያለውን በወረርሽኙ ተጠቂዎች ቁጥር ካየን በአንዳንድ ወረዳዎች እየጨመረ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ›› ያሉት ዳይሬክተሩ፣ ለአብትም በምሥራቅ ቦረና፣ በጉጂ፣ ምዕራብ አርሲ፣ ምሥራቅ ባሌ አሁንም የኮሌራ ወረርሽኝን መቆጣጠር እንዳልተቻለና የተጠቂዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
‹‹በክልላችን የተለያዩ ወረዳዎች ወረርሽኞች አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ኩፍኝና ኮሌራን መጥቀስ ይቻላል፡፡ የኮሌራን ሁኔታ ስንመለከት ግን አሁንም በክልሉ በሚገኙ ስድስት ዞኖችና 17 ወረዳዎች ሥርጭቱ አለ፡፡ መቆጣጠርም አልተቻለም›› ሲሉም አክለዋል፡፡
ዳይሬክተሩ ለሪፖርተር ያስረዱት፣ ወረርሽኙ የተከሰተው በነሐሴ ወር 2014 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ እንደሆነ፣ በዚህም ስምንት ወር እንዳስቆጠረና በሁሉም ወረዳዎች በመሠራጨቱ መቆጣጠር እንዳልተቻለ፣ በክልሉ በሚገኙ 25 ወረዳዎች 4,165 የሚሆኑ ሰዎች በወረርሽኙ በመጠቃታቸው ከማኅበረሰቡ እንደተለዩ ነው፡፡
የኮሌራ ወረርሽኝ በክልሉ በሚገኙ 25 ወረዳዎች ተስፋፍቶ እንደነበር የገለጹት አቶ ገመቹ፣ አሁንም ቢሆን ስምንት ወረዳዎችን መቆጣጠር ቢቻልም በ17 ወረዳዎች ያለውን የወረርሽኙን ሥርጭት መቆጣጠር እንዳልተቻለ ገልጸዋል፡፡
በኮሌራ ወረርሽኝ የሚጠቁ ሰዎች ቁጥር በየወሩ በስንት እንደጨመረ ማብራሪያ እንዲሰጡ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄም፣ ትክክለኛ ቁጥሩን እንደማያስታውሱ፣ ባለፉት ሦስት ወራት ያለው የተጠቂዎች ቁጥር ግን ጨምሯል ብሎ መውሰድ እንደሚቻል፣ በየወሩ ያለው ቁጥር ቢጨምረም ከ15 ቀን ወዲህ ያለው በየቀኑ የሚስተዋለው ወደ ሕክምና የሚመጡ ሰዎች ቁጥር ግን እየቀነሰ መሆኑን አቶ ገመቹ አስረድተዋል፡፡
‹‹በተለይ ከ15 ቀን ወዲህ በየቀኑ ያለው የሕሙማን ቁጥር የመቀነስ ነገር አሳይቷል፡፡ ከ15 ቀን በፊት ያለው መረጃ የሚያሳየው በምሥራቅ ቦረና፣ በጉጂ፣ በቀን ከ40 እስከ 50 ታካሚዎች ይመጡ ነበር፡፡ አሁን ግን በቀን ወደ ሕክምና የሚመጡት ሰዎች ቁጥር ወደ 30 ዝቅ ብሏል›› ብለዋል ዳይሬክተሩ፡፡
እንደ ገለጻው ከሆነ፣ ከኮሌራ ወረርሽን በተጨማሪ የኩፍኝ ወረርሽኝም ማኅበረሰቡን እያጠቃ መሆኑ ተመላክቷል፡፡ ‹‹ባለፉት ዘጠኝ ወራት 4,209 የሚሆኑ የኩፍኝ ሕሙማን ተለይተዋል፡፡ ይህ የታማሚዎች ቁጥር የተገኘው በክልሉ በዘጠኝ ዞኖችና በ38 ወረዳዎች ነው›› ብለዋል አቶ ገመቹ፡፡ በአሁኑ ወቅት በተለይ 12 ወረዳዎች ላይ አልፎ አልፎ የኩፍኝ ሥርጭት እንደሚስተዋል አክለዋል፡፡
በኩፍኝና በኮሌራ ወረርሽኝ የስንት ሰዎች ሕይወት እንዳለፈ ምላሽ እንዲሰጡ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄም፣ በኮሌራ ወረርሽኝ ከ50 በላይ፣ በኩፍኝ ከ30 በላይ በአጠቃለይ ከ80 በላይ ሰዎች ሕይወት እንዳለፈ አስረድተዋል፡፡
በክልሉ በአጠቃላይ ከስምንት ሺሕ በላይ ሰዎች በኮሌራና በኩፍኝ ወረርሽኝ እንደተጠቁ የገለጹት አቶ ገመቹ፣ ኮሌራንና ከፍኝን ለመከላከል የሕክምና ማዕከላት መቋቋሙን፣ ድርቅና የፀጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች የንጹህ መጠጥ ውኃ የማዳረስ ሥራ እየተሠራ መሆኑን፣ የክትባት አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል፡፡