የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም በደቡብ ኦሞ ዞን በተከሰተው ድርቅና ጎርፍ አደጋ ምክንያት፣ የፌዴራል መንግሥቱ ለችግሩ ምላሽ እንዲሰጥ የክልሉ ፕሬዚዳንትን ጨምሮ ከፍተኛ የክልሉ የሥራ ኃላፊዎች ስድስት ጊዜ በደብዳቤ እንዲሁም በስልክ ዕርዳታ ቢጠይቁም፣ ምንም ዓይነት መልስ አለመሰጠቱን በምርመራ ሥራዬ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
የሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም በኦሮሚያ፣ በደቡብና በሶማሌ ክልሎች፣ በቦረና፣ በደቡብ ኦሞና በዳዋ ዞኖች አካባቢ በድርቅና ጎርፍ ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች የሚደረግ ሰብዓዊና ቁሳዊ ድጋፍ፣ መሠረታዊ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥና መልሶ የማቋቋም ሥራ ያለበትን ደረጃ በተመለከተ አካሄድኩት ያለውን የቁጥጥር ሥራ አስመልክቶ ሚያዝያ 19 ቀን 2015 ዓ.ም. መግለጫ ሰጥቷል፡፡
በሦስቱ ክልሎች በሚገኙ ሦስት ዞኖች እስካሁን በድርቅ ሳቢያ የተፈናቀሉ 243 ሺሕ ነዋሪዎች በመጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ እንደሚገኙም ተገልጿል፡፡ በድርቅና ጎርፍ የደረሰው ጉዳት ሲታይ በኦሮሚያ ቦረና ዞን 1.32 ሚሊዮን እንስሳት መሞታቸውን፣ በሶማሌ ዳዋ ዞን 335 ሺሕ ገደማ እንስሳት ሲሞቱ፣ 420 ሺሕ ገደማ የሚሆኑት አደጋ ላይ መውደቃቸውን እንዲሁም በደቡብ ኦሞ ዞን በድርቅና በጎርፍ የሞቱ እንስሳት 48 ሺሕ ናቸው ተብሏል፡፡
በደብብ ክልል በተፈጠረው ድርቅና ጎርፍ ምክንያት የደረሰውን ሁኔታ የሚያሳይ አጠቃላይ የመረጃ ችግር ቢኖርም፣ ደቡብ ኦሞ ዞን 338 ሺሕ የሚጠጋ ሕዝብ ለጉዳት መዳረጉን ከተገኘው በምርመራ ሥራው መረጋገጡ ተገልጿል፡፡
በድርቅና ጎርፍ አደጋው ለተጎዱ ዜጎች በወረዳና በዞን እንዲሁም ከክልል በኩል ድጋፍ ይደረግ የነበረ ቢሆንም፣ ለስድስት ጊዜ ያህል ለፌዴራል መንግሥት ደብዳቤ ቢጻፍም የፌዴራል መንግሥት መልስ መስጠት አለመቻሉን የዕንባ ጠባቂ ተቋም የአስተዳደር በደል መከላከል ዳይሬክተር አቶ አዳነ በላይ አስታውቀዋል፡፡
የተጠናቀረው ሪፖርት እንደሚያሳየው ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሔ እንዲሰጥበት ለፌዴራል አደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ኮሚሽን ደብዳቤና በስልክ ንግግር ቢደረግም ይሰጥ የነበረው ምክንያት ግን የጨረታ ግዥ ጋር የተያያዘ እንደነበር ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ለዞኑ ይመጣ የነበረው ዕርዳታ ለማግኘት ሲሉ ትክክለኛ ያልሆነ መረጃ መስጠትና የአካባቢው አመራር ጭምር ዕርዳታ ለማግኘት ፍላጎት ያሳዩ እንደነበር ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ተቋሙ ከመጋቢት 11 እስከ መጋቢት 25 በዞኖቹ አካሄድኩት ባለው ጥናት በሦስቱም ክልሎች በተካሄደው የቁጥር ሥራ እንደሚያሳው፣ በሁሉም አካባቢዎች የተደራጀ መረጃ አለመኖር የድርቁንና የጎርፍ አደጋው የፈጠረውን ግልጽ ሥዕላዊ መረጃ ወጥ በሆነ መልኩ ማግኘት አልተቻለም፡፡
ይሁን እንጂ የቁጥጥር ሥራው እስከተከናወነበት ድረስ በድርቁና በጎርፍ አደጋ ምክንያት የሞተ ሰው ማግኘት እንዳልቻለ ጥንቅሩ ያመላከተ ሲሆን፣ የጎርፍና የድርቅን አደጋ ተከትሎ በሚመጡ በሽታዎች ሊሞቱ የሚችሉ ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ግን አንስቷል፡፡
ድርቁን መቀነስ የሚቻል የነበረ ቢሆንም፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራው በተገቢው መልኩ ባለማከናወኑ ችግሩን እንዳባባሰው፣ ችግሩ ከተከሰተ ወዲህም በመንግሥትና በሌሎች የሚመለከታቸው ተቋማት መካከል የነበረው የኮሙዩኒኬሽንና ቅንጅታዊ አሠራር አናሳ መሆን ድርቁንም ይሁን የጎርፍ አደጋውን አባብሶታል ተብሏል፡፡