‹‹ይህ መጽሐፍ በይነሲፕሊናዊና ሥነመለኮታዊ አሰላስሎት በታዋቂው ኢትዮጵያዊ ፊልም ሠሪና ዳይሬክተር፣ ጸሐፊና ፕሮፌሰር፣ ታሪክ ነጋሪ ኃይሌ ገሪማ ሲኒማ ዙሪያ ያጠነጥናል። ኃይሌ የአፍሪካን ሥነቃል እና ሌሎች የሥነጥበብ ዓይነቶችን ወደ ሲኒማ ቋንቋ ለውጦታል። ኃይሌ ገሪማ ለአምስት ምዕት ዓመታት ፊልም በሠራቸው የፓን አፍሪካን ፊልሞቹ የእምቢባይነት ተምሳሌት በመሆን አፍሪካን ዝቅ የሚያደርጉ የተሳሳቱ አፍሪካውያንን ዝቅ የሚያደርጉ የድኅረ ቅኝ ግዛት አስተሳሰቦችን ተቃውሞአል…፤›› የሚለው በባህር ማዶ <Stories from the Fireplace Theological Meditations on Haile Gerima`s Cinema> (የእሳት ዳር ተረኮች/ታሪኮች ሥነመለኮታዊ ማሰላሰሎች በኃይሌ ገሪማ ፊልሞች ላይ) በሚል ርዕስ የምርምር ሥራውን የሠራው በሴንት ሉዊስ ኮንኮርዲያ ዩኒቨርሲቲ የሦስተኛ ዲግሪ ተማሪና በጥበብ የጽሞና እና ምርምር ማዕከል ተመራማሪ ተክለ ጻድቅ በላቸው ነው፡፡
አዘጋጁ በመጽሐፉ የጀርባ ሽፋን ላይ እንደገለጸው፣ ኃይሌ ገሪማ የድኅረ ቅኝ ግዛት አስተሳሰቦችን ሲቃወም፣ በምላሹም ካሜራን እንደመሣሪያ ታዋቂው እንደ ሆሊውድ መሰል ሲኒማ የፈጠረውን መገለልን ከራስ ጋር ባይተዋርነትን ለመቃወም አውሎታል። በምትኩም በተንቀሳቃሽ ምስል የከበረ አፍሪካዊ ምስልን በማቆም ሲኒማን ከቅኝ ግዛት ነጻ የማውጣት (ዲኮሎናይዜሽን) እና አዕምሮን ከተገዥነት ነጻ የማውጣት ትግል እያካሄድ ይገኛል።
በዚህ የኅትመት ውጤት ላይ ውይይት ለማካሄድ፣ የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ የሥነ ጥበባት ማዕከል በሳይንስ አካዴሚ ለቅዳሜ ሚያዝያ 21 ቀን 2015 ዓ.ም ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ ቀጠሮ ይዟል፡፡
በዕለቱ ለውይይት መነሻ ሐሳብ የሚያቀርቡት አባ ዳንኤል አሰፋ (ዶ/ር) ሲሆኑ ተወያዮቹ ተክለ ጻድቅ በላቸው (ጸሐፊው)፣ ትዕግስት ዓለማየሁና ምኒልክ መርዕድ ናቸው፡፡
በጸሐፊው ተክለ ጻድቅ በላቸው አገላለጽ፣ የፕሮፌሰር ኃይሌ የትዝታ ወይም የትውስታ ፊልሞቹም የትውልደና የዘረ አፍሪካንን ታሪኮች በትጋት ዘግቦአል። ኃይሌ ከታላላቆቹ የአፍሪካ ፊልም ሠሪዎች ማለትም ከአፍሪካ የፊልም አባት ከኦስማን ሴምቤንና ከሜድ ሆንዶ የሚመደብ መሆኑ ተጨማሪ በይነዲሲፒሊናዊ ጥናት እንደሚያሻው ያመላክታል።
‹‹የኃይሌ ትሪያንጉላር ወይም ሦስትዮሽ ሲኒማ እንዲሁም ኢፍጹማዊ ሲኒማ የሚሉት ፍልስፍናዎቹና ሞዴሎቹ መነሻቸው ከአገር በቀል እሴቶችና የባህል ምርቶች ለምሳሌ ከቅዱሳት ሥዕላት እና የእሳት ዳር ወጎች የሚመነጩ ናቸው። ሥራዎቹ የራስን ማንነት ስለማጽናት፤ ልዩነቶችን አለመፍራት ልክ እንደኡቡንቱ ዓይነት ሰውኛ መስተጋብርንም ስለማስረጽ ያስረዳሉ፤›› ሲልም ያክላል፡፡
የምርምር መጽሐፉ በኃይሌ ሥራዎችና አሰተሳሰቦቹ በኩል አፍሪካን እንደገና በሲኒማ መስኮት በኩል በመመልከት አፍሪካዊ መሆንን እየሆኑ ማደግን እንድናሰላስል ይጋብዛሉ ሲልም ያመሰጥራል።