በአበበ ፍቅር
ከሁለት ሳምንታት በላይ ያስቆጠረው የኢንተርኔት (የበይነ መረብ) አገልግሎት መቋረጥ በትምህርታቸው ላይ ጨና እየፈጠረባቸው መሆኑን፣ የወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ተናገሩ፡፡
የተለያዩ መረጃዎችን በብዛት የሚያገኙት ከኢንተርኔት መሆኑን የተናገሩት ተማሪዎቹ፣ አሁን ግን አገልግሎቱ ሙሉ በሙሉ በመቋረጡ ከመምህራን የሚሰጣቸውን የቤት ሥራም ሆነ በግላቸው የሚፈልጉትን ወቅታዊ መረጃ ለማግኘት መቸገራቸውን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
የወልዲያ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት የጋዜጠኝነትና የተግባቦት ትምህርት ክፍል ተማሪ የሆነው ሶፎኒያስ ብርሃኑ እንዳለው፣ ላለፉት ሁለት ሳምንታት የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ በኢንተርኔትም ሆነ በቴሌግራም መረጃዎችን ማግኘት አልተቻለም፡፡
በመሆኑም እሱና ጓደኞቹ ማጣቀሻ መጻሕፍትንና መረጃዎችን ለማግኘት መቸገራቸውንና ሥራቸውን በወቅቱ ሠርተው ማስረከብ እንዳልቻሉ አስረድቷል፡፡
ምንም እንኳን ከየካቲት ወር ጀምሮ በመላ አገሪቱ የኢንተርኔት አገልግሎት የተቋረጠ ቢሆንም፣ ቪፒኤንና ፒስፎን በተባሉ መተግበሪያዎች በመታገዝ የተለያዩ መረጃዎችን ሲጠቀም እንደነበር የተናገረው ሌላው ተማሪ አብርሃም የኋላው፣ ካለፉት ሁለት ሳምንታት ጀምሮ ግን አገልግሎቱ ሙሉ በሙሉ መቋረጡን ተናግሯል፡፡
በተለይ የመመረቂያ ጽሑፍ ለማዘጋጀት ከመቼውም ጊዜ በላይ እንደተቸገሩ የተናገረው አብርሃም፣ ወደ ከተማ በመሄድ በሆቴሎች ውስን የዋይፋይ አገልግሎት ለመጠቀም መገደዳቸውን አክሏል፡፡
በሌላ በኩል ወልድያ ከተማን ጨምሮ በቆቦና በአላማጣ ከተሞች የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጡን ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡
በአላማጣ ከተማ አገልግሎቱ ከተቋረጠ ከአንድ ወር በላይ እንዳስቆጠረ መሠረት ፀጋዬ የተባለች ነዋሪ ገልጻለች፡፡
ወቅቱ የዲጂታል እንደ መሆኑ ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት ኢንተርኔት በእጅጉ አስፈላጊ ነው ያለችው መሠረት፣ አሁን ግን ምንም ዓይነት የኢንተርኔት አገልግሎት ማግኘት ባለመቻላቸው መቸገራቸውን አስረድታለች፡፡
በተመሳሳይ የቆቦና የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ፣ በኢንተርኔት ታግዘው ሥራዎችን ለማከናወን እንደቸገሩ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
የኢንተርኔት አገልግሎት እንደተቋረጠ የወልዲያ ከተማ ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራራ አረጋግጠዋል፡፡
አገልግሎቱ በምን ምክንያት እንደተቋረጠ መረጃው እንደሌላቸው የተናገሩት አቶ ዱባለ፣ ነገር ግን ‹‹ከደኅንነት ጋር ተያይዞ ሊሆን ይችላል፤›› ብለዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ ከኢትዮ ቴሌኮም ማብራሪያ ለማግኘት ሙከራ ቢደረግም ምላሽ ማግኘት አልተቻለም፡፡