ከመንግሥትና ከግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በልዩ ልዩ የጤና ሙያ በመጀመሪያ ዲግሪ ተመርቀው ወደ ሥራ ከመሠማራታቸው በፊት የሙያ ብቃት ምዘና ከወሰዱ 19,681 የሕክምና ባለሙያዎች መካከል 8,993 ወይም 45 በመቶ ያህሉ ብቻ ማለፋቸውን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በሚኒስቴሩ የጤናና ጤና ነክ ተቋማትና ባለሙያዎች ቁጥጥር ኤክስኪዩቲቭ ቢሮ የፈተና ዝግጅት ዴስክ ኃላፊ ሜሮን ያዕቆብ (ዶ/ር) በተለይ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ካልተሳካላቸው ተፈታኞች ሌላ በፈተናው ሒደት ላይ የደምብ ጥሰት ሲፈጽሙ የተደረሰባቸው 40 ባለሙያዎች ፈተናውን እንዳይወስዱ ተደርገዋል፡፡
ከፈተና የተባረሩ ባለሙያዎች ሲፈጽሙ ከተደረሰባቸው የደምብ ጥሰቶች መካከል የኤልክትሮኒክስ መሣሪያዎች ማለትም ሞባይል ይዞ በመግባትና በፈተናው ጊዜ መጠቀም፣ በወረቀት ለሌላው ማቀበል፣ ተፈታኝ ያልሆኑ ሰዎች ፈተና ክፍል ገብተው ለሌላ መፈተን እንደሚገኙበትም ሜሮን (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
በፈተናው ወቅት የሚያጋጥሙ የደምብ ጥሰቶችን ለመከላከል እንዲቻል በየፈተና ጣቢያዎቹ የመፈተሻ ማሽን እንደገባ፣ ሆኖም ተፈታኞች ማሽኑን አልፈው ፈተና ክፍል ውስጥ ገብተው በሞባይል ሲጠቀሙ እንደተደረሰባቸው አክለዋል፡፡
የሙያ ብቃት ምዘና ፈተናን ያለፉ የጤና ባለሙያዎች ፍቃዳቸውን ተቀብለው ሥራ የመቀጠር ዕድላቸው የሰፋ ሲሆን፣ ያልተሳካላቸው ደግሞ እንደገና የመፈተን መብት ያላቸው መሆኑን ገልጸው፣ ተፈታኝ ሳይሆኑ መፈተን ላለበት ባለሙያ ሲፈተኑ የተደረሰባቸው የጤና ባለሙያዎች በጤና ባለሙያዎች የሥነ ምግባር ኮሚቴ በኩል ክስ እንደሚቀርብባቸው አስረድተዋል፡፡
ኃላፊዋ እንዳሉት፣ ለፈተና የቀረቡት ጥያቄዎች ተመራቂዎቹ በሥልጠና ላይ በቆዩባቸው ዓመታት በተከታተሉዋቸው 13 የሙያ ዓይነቶች ላይ የተመሠረቱ ናቸው፡፡
የፈተና ዓይነቶቹ ሜዲስን፣ ፐብሊክ ሔልዝ፣ ነርሲንግ፣ ሚዲዋይፍሪ፣ ፋርማሲ፣ ሜዲካል ላብራቶሪ ሳይንስ፣ አንስቴዥያ፣ ዴንታል ሜዲስን፣ ሜዲካል ራዲዮሎጂ ቴክኖሎጂ፣ ፒዴያትሪክ ኤንድ ቻይልደ ሄልዝ፣ ሳይካትሪክ፣ ኢመርጀንሲ ኤንድ ክሪቲካል ኬር ነርሲንግና ኢንቫይሮመንታል ሔልዝ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡
በኢትዮጵያ የጤና ባለሙያዎች የሙያ ብቃት ምዘና ፈተና መስጠት የተጀመረው ሐምሌ 2011 ዓ.ም. ሲሆን፣ የአሁኖቹን ጨምሮ እስካሁን ድረስ የተፈተኑት ሙያተኞች ብዛት 115,553 ነው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ፈተናውን በሚገባ ያለፉ 51,745 ወይም 44.8 በመቶ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
እንደ ሜሮን (ዶ/ር)፣ የጤና ሚኒስቴር የኢትዮጵያን ሕዝብ ጤና ከሚያስጠብቅበት ዕቅድ ውስጥ አንዱና ዋነኛው ስትራቴጂ ሆኖ የተቀመጠው ቁጥጥር ነው፡፡ ይህንንም ማድረግ ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት የጤና ባለሙያዎች ተወዳዳሪና በሥነ ምግባር የታነፁ እንዲሆኑና የሚያስፈልጋቸውን ክህሎትና ዕውቀት እንዲይዙ ለማድረግ ነው፡፡
በፈተናው አዘገጃጀትና አሰጣጥ ሒደቶች ላይ በርካታ ተግዳሮቶች እንደተከሰቱ፣ ከእነዚህም መካከል ፈተናዎቹ በተለያዩ ምክንያት በመዘግየታቸው የተነሳ በታሰበውና በታቀደላቸው ጊዜ አለመስጠት፣ ውጤቶቹም በጊዜው አለመሠራጨታቸውና ይህም ፈተናውን ያለፉ ወደ ሥራ እንዲገቡ የማድረጉ እንቅስቃሴ ላይ መጓተትን እንዳስከተለ አመልክተዋል፡፡
‹‹እኛ አገር ዱሮ ዱሮ ተማሪዎች እያለን ነርሶች ትምህርታቸውን ሲጨርሱ አገራዊ ፈተና ነበራቸው፡፡ ለዚህም ተቋማቱና ተመራቂዎቹ የየራሳቸውን ዝግጅቶች ያደርጉ ነበር፡፡ ይህም ለትምህርቱ ጥራት የራሱ አስተዋጽኦ አለው፤›› ያሉት ደግሞ የጤና ሚኒስቴር ዋና አማካሪ ከበደ ወርቁ (ዶ/ር) ናቸው፡፡
እንደ አማካሪው አባባል የሙያ ብቃት ምዘና ፈተና ዋናው ዓላማ ብቃት ያለውን ባለሙያ ለማሠራትና ጤናን ከማጎልበት አንፃር ማኅበረሰቡን ወይም ሕዝቡን ለመጠበቅ ነው፡፡