ተግባራዊ መደረግ በጀመረው አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት ከተጨመሩ የትምህርት ዓይነቶች አንዱ የክወናና የዕይታ ጥበባት ትምህርት ይገኝበታል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃ የተዘጋጀው የመማርያ መጽሐፍም ከስድስተኛ ክፍል በታች ላሉት በአማርኛ ሰባትና ስምንት ደግሞ በእንግሊዝኛ ሲሆን፣ በይዘቱም የሙዚቃ መሠረታዊ ኖታዎች፣ ሥነ ውበት፣ የሙዚቃ ጥመርታ ዝምድናና ትግበራ እንዲሁም ተያያዥ የሆኑ ርዕሰ ጉዳዮችን ይዟል፡፡
የመጽሐፉ ይዘት በንድፈ ሐሳብና በተግባር እንዲሰጡ ተደርጎ የቀረጸም ነው፡፡ ነገር ግን ትምህርቱ በመጽሐፉ እንደተቀመጠው ከመስጠት አንጻር በአብዛኞቹ ትምህርት ቤቶች የመምህራንም ሆነ የግብዓት እጥረት ይታያል፡፡
በመምህራን በኩል ያሉ ክፍተቶችን ለመሙላት ደግሞ የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ፣ ከሁሉም ክፍለ ከተሞች ከሚገኙ ትምህርት ቤቶች ተውጣጥተው ሥልጠና ሲወስዱ የነበሩ መምህራንን አስመርቋል፡፡
ለሦስተኛ ዙር በተሰጠው ሥልጠናም ከ350 በላይ የአንደኛ ደረጃ የኪነ ጥበብ መምህራን ተካፍለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ ሥነ-ጥበባትና ዲዛይን ትምህርት ቤትና ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ጋር በመተባበር ለሥነ-ሥዕልና ሙዚቃ መምህራን ሥልጠናውን መስጠታቸውን የቢሮው የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ኃላፊ ሰርፀ ፍሬስብሃት ተናግረዋል፡፡
ከቀለም ትምህርት ባሻገር በኪነ-ጥበብ ትውልድን የማነፅ ሥራ መሥራት አስፈላጊ ነው ያሉት ኃላፊው፣ ሙያውን የላቀ ለማድረግ ከትምህርት ተቋማት ጋር መሥራትና ተቋማዊ ዕውቀትን መጠቀም ሥነ-ጥበቡን የበለጠ ለማበልፀግ እንደሚረዳ ጠቁመዋል።
መምህራን በዘርፉ የትምህርት ዕድል አለመኖሩን የገለጹ ሲሆን፣ ለመምህራን በዘርፉ የሚሰጥ ሥልጠናና ትምህርትን ቢሮው ቢያስተባብር የሚል ጥያቄም አንስተዋል፡፡
በኪነ-ጥበብ ማስተማሪያ መጽሐፍት ላይ የይዘት ማስተካከያ እንደሚያስፈልግ ከሠልጣኝ መምህራን የተነሳ ሲሆን፣ ቢሮው ፍተሻ ለማድረግ ከባለሙያዎች ጋር ሆኖ መሥራት እንዳለበት አቶ ሰርፀ አሳውቀዋል።
በቢሮው የኪነ-ጥበብ ኢንዱስትሪ ማበልፀግና ማስፋፋት ዳይሬክተር አቶ አስቻለው ቦጋለ እንዳሉት፣ ቢሮው ከትምህርት ቢሮ ጋር በመተግባር በቀጣይ እስከ ወረዳ ባለው ተዋረድ በቴአትርና ሌሎች ተያያዠ ኪነ-ጥበባዊ የሙያ ማካካሻ ሥልጠና ለመስጠት ይችላል፡፡