ቀኑ ሲጨላልም
ክረምቱ ሲገባ
ተነሱ እረሱ
ሲሉን በጥሩንባ
ወጣን በትካዜ
መጣን በሰቀቀን
ከዘር ማንዘር መሐል
አንዲት ዘር ፈልቅቀን፡፡
በዕንባችን ዝናብ
መሬቱን አርሰን
በዋይታችን ሞፈር
ጓሉን አፈራርሰን
ባራሽ ገበሬ ወግ
በዘር ውርዋሬ
ቆፍረን ዘራነው
ያንን የሳቅ ፍሬ
ዘርተን ሳንመለስ
ወግተን ሳንነቅል
የዘራነውን ሳቅ
አየነው ሲበቅል፡፡
አየነው! ለየነው!
ቆመን ከዚያው ሥፍራ
ዝምታን አሽቶ
ዝምታን ሲያፈራ፡፡
- ታገል ሰይፉ ‹‹ቀፎውን አትንኩት›› (1986 ዓ.ም.)