የአየርላንድ፣ የሰሜን አየርላንድ እና የብሪታንያ ህዝቦች ሚያዚያ 2 ቀን 2015 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. ኤፕሪል 10 ቀን 2023 ዓ.ም.) በአየርላንድ ደሴት ውስጥ የተለያዩ ፖለቲካዊ ልማዶች ያሏቸው መሪዎች ከያሉበት በመሰባሰብ የጉድ ፍራይዴይ ስምምነትን የፈረሙበትን 25ኛ አመት የአየርላንድ ደሴት የፖለቲካ ያከብራሉ። ልክ እንደ ኢትዮጵያው ጠላትነትን በዘላቂነት የማቆም ስምምነት ሁሉ፣ የጉድ ፍራይዴይ የሰላም ስምምነትም እንደ አንድ ታላቅ ኩነት ውዳሴን ተችሯል። ይኽ የጉድ ፍራይዴይ ስምምነት ለአየርላንድ እና ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) የሰላም፣ የጸጥታ እና የመረጋጋት ዘመንን አምጥቷል፣ ማህበረሰቦችን ከፋፍሎ የብዙዎችን ህይወት ያለጊዜያቸው ያጠፋውን የ 30 አመታት አሰቃቂ የግጭት ምዕራፍን ዘግቷል። ስምምነቱ የአመጽና የሁከት ፖለቲካን ውድቅ ለማድረግ እና የማንነት ብዝሃነትን እና የአየርላንድን የሰሜን እና ደቡብ ህዝቦችን ፍላጎት ያቀፈ ግንኙነት አዲስ ማዕቀፍ ለመፍጠር የተደረገ ውሳኔ ነበር።
ስምምነቱ በአየርላንድ እና በእንግሊዝ የጋራ ታሪክ ውስጥ ልዩና ወሳኝ ከመሆኑም ባሻገር ለህዝባችን የተሻለ የወደፊት ሁኔታን ለማረጋገጥ በደሴቶቻችን ውስጥ እና መካከል ያለውን ግንኙነት ለመለወጥ የጋራ ቁርጠኝነትን ያሳያል። አሁን ከ 25 አመታት በኋላም፣ ይኽንን ድንቅ ድል ማክበራችን እና አየርላንድ የ 1990 አመተ ምህረቱን የርዕይ መንፈስንና አመራሯን ዛሬ ላይ እያጋጠሙ ላሉት አለም አቀፋዊ ተግዳሮቶች እንዴት አድርጋ እንደምታጋራ ማሰቧ በእርግጥም ትክክለኛ ነገር ነው።
ባለፉት 25 ዓመታት፣ ሰላም እና እርቅ ሊመጣ የሚችለው ግጭት ውስጥ ያሉ ወገኖች ልዩነታቸውን ወደ ጎን በመተው ለሁሉም መሻሻል ሲሰሩ ብቻ እንደሆነ አየርላንድ ተገንዝባለች። የሰሜን አየርላንዱ የሰላም አቀንቃኝ ጆን ሂዩም የጉድ ፍራይዴይ የሰላም ስምምነትን እውን ለማድረግ ባደረጉት ጉልህ አበርክቶ የሰላም የኖቤል ሽልማታቸውን ሲቀበሉ በአጽናኦት እንደተናገሩትም፣ “ልዩነት የሰብአዊ ፍጡር መለያ ማንነቱ ነው። ለልዩነት የሚሰጠው ምላሽ ልዩነትን ማክበር ነው። እዚህ ውስጥም መሰረታዊው የሰላም መርሆ ይገኛል – ብዘሃነትን ማክበር።”
እነዚህ መርሆዎች ሰላምን በመገንባት ሂደት ውስጥ ሁሉም ድምፆች መደመጣቸውን እና መከበራቸውን ማረጋገጥ አለባቸው። በሰሜን አየርላንድ ውስጥ በተለይ የሴቶች ድምጾች ያለመደመጥ አደጋ ውስጥ መደቃቸውን ተረድተናል። የሰሜን አየርላንድ ሴቶች ዜጎች በሰላሙ ሂደት ውስጥ የሚገባቸውን ቦታቸውን ለማግኘት መታገል ነበረባቸው፤ ተገቢ ቦታቸውን ባገኙ ጊዜም ሰላምን ለማስፈን እና ለማስቀጠል ግዙፍ አስተዋፅዖን ለማበርከት ችለዋል። የሴቶች ድምፅ ችላ አለመባሉን ማረጋገጥ በጣም አስፈላጊ ነው – ሴቶችን ፣ ወጣቶችን እና ብዝሃ የፖለቲካ አስተያየቶችን ያላካተተ ሂደት ለዘላቂ ሰላም ጠንካራ መሠረት ሊሆን አይችልም።
በሰሜን አየርላንድ ውስጥ የሰላም ሂደቶች የሳምንታትን፣ የወራትን፣ የዓመታትን ግዙፍ፣ ቀጣይነት ያለው ጥረት፣ ጽናት፣ ትዕግስት እና እምነት እንደሚፈልጉም ተገንዝበናል። በወሳኝ መልኩ፣ ይህ ቁርጠኝነት አዎንታዊ ምላሹን ያገኘው ሚያዚያ 2 ቀን 1990 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. ኤፕሪል 10 ቀን 1998 ዓ.ም.) አዲስ እውነት ሲመሰረት ነበር። ይኽ የጉድ ፍራይዴይ የሰላም ስምምነት – የማይመስል፣ የማይቻል ይመስል የነበረው ስምምነት – በእርግጥም የሚቻል መሆኑን አሳይቷል። ይኽ ሁል ጊዜም የተስፋ እና የመጽናኛ ምንጭ እና በሰላም ላይ ያለው እምነትም ከማንኛውም አማራጭ የተሻለ ለመሆኑ እንደ አንድ መነሳሻ ሆኖ መዝለቅ አለበት።
ሆኖም ግን፣ ከ 25 አመታትም በኋላ፣ ታሪካዊ ክስተቶችን ማወደሱ ብቻ አደጋ ሊኖረው ይችላል። የጉድ ፍራይዴይ የሰላም ስምምነት ፍጹም አለመሆኑን ማስታወስ አስፈላጊ ነው። የትኛውም የሰላም ስምምነት ፍጹም አይደለም። የአየርላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚ/ር የሆኑት ማይክል ማርቲን በቅርቡ እንደተናገሩት፣ “የትኛውም የአየርላንድ ማህበረሰብ በ 1990ው ስምምነት የተመኛቸውን ሁሉ አላገኘም፣ እያንዳንዱ ሰው ግን ሰላምን አግኝቷል። የጉድ ፍራይዴይ የሰላም ስምምነት መፈረም ጅማሮም ፍጻሜም ነበር። የስምምነቱ መፈረም ሁሉም ወገኖች ለአመታት ያከናወኗቸው ጠንካራ ስራዎች እና አስቸጋሪ ሰጥቶ መቀበሎች ፍጻሜ ያገኙበት ነበር። የስምምነቱ መፈረም የሰላም ግንባታ፣ የእርቅ እና ለተለየ ግን ደግሞ እጅግ ለተሻለ መጻኢ ጊዜ አዲስ ሂደት ጅማሮም ነበር።”
ኢትዮጵያም አስደናቂ ድል የሆነውን የራሷን ጠላትነቶችን በዘላቂነት የማቆም ስምምነት በምታስብበትም ወቅት፣ አየርላንድ በሰሜን ኢትዮጵያ የተከሰተውን ሁከትና ብጥብጥ ማብቃቱን እና የተሻለች ኢትዮጵያን ለሁሉም ተጠቃሚ እንድትሆን በሁሉም ወገን ያለውን ቁርጠኝነት በደስታ ትቀበላለች። ከግጭት በኋላ በማንኛውም የድህረ-ግጭት አውድ ውስጥ ስሜታዊ፣ ባህላዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና አካላዊ ጠባሳዎቹ ስር ይሰዳሉ። አስቸጋሪው እርቅን እውን የማድረግ ስራ በርካታ አመታትን እና ከፍተኛ ጥረትን ይጠይቃል። የሚነሱትን ችግሮች ሁሉ ተቋቁሞ ሰላም እንዲጠበቅ ማድረግ የእኛ ኢትዮጵያ ውስጥ የምንኖር ሰዎች ግዴታና ኃላፊነት ነው። አየርላንድ የሰላም ስምምነቱ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲሆን ለመደገፍ እና ለመላው ኢትዮጵያውያንም ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ የበኩሏን አስተዋጽኦ ለማድረግ ዝግጁ ነች።