- የምግብ ዋስትና ማጣትና የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ሥር የሰደዱ ችግሮች ሆነዋል
በኢትዮጵያ ያለው ድህነት ባለፉት ሁለት አሠርታት ቢቀንስም፣ ከአራት ቤተሰቦች አንዱ ቤተሰብ ወይም 24.8 በመቶ ሕዝብ ከድህነት ወለል በታች እንደሚኖር የግሎባል ሃንገር ኢንዴክስ 2022 አመልክቷል፡፡
መጋቢት 28 ቀን 2015 ዓ.ም. ይፋ የተደረገው ግሎባል ሃንገር ኢንዴክስ እንዳመለከተው፣ በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ድህነትን በመቀነሱ ረገድ ተመዝግቦ የነበረው ዕድገት የተቀለበሰው ድርቅ፣ የበረሃ አንበጣ፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ያስከተለው የኢኮኖሚ ጫና፣ የምግብ፣ የማዳበሪያና የነዳጅ ዋጋ መጨመር በተለይ ደግሞ በግጭት ምክንያት ነው፡፡
ድህነቱ በርካታ ኢትዮጵያውያን ተለያይነት ያላቸው ምግቦች እንዳይገዙ ያደረገ መሆኑን የጠቀሰው ኢንዴክሱ፣ 25 በመቶ የሚሆኑ ግለሰቦች የምግብ ዋስትና እንደሌላቸው፣ ይህም ከሰሃራ በታች የሚገኙ የአፍሪካ አገሮች በአማካይ ካላቸው የ18 በመቶ የምግብ ዋስትና ማጣት በእጅጉ የላቀ እንደሆነም ጠቁሟል፡፡
እንደ ኢንዴክሱ፣ በኢትዮጵያ ተለያይነት ያላቸውን ምግቦች ማምረት እየጨመረ ቢመጣም፣ ከታረሰው መሬት ውስጥ 75 በመቶ ያህሉን እህል ይይዛል፡፡ 60 በመቶ ያህሉ የግብርና ውጤቶችም የእህል ዓይነቶች ናቸው፡፡ ይህም በኢትዮጵያ ዝቅተኛ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የእንስሳትንና የእንስሳት ተዋጽኦ ዝቅተኛ አመጋገብ እንዲኖር አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ ሥርዓት በምርትና በምርታማነት እጥረት፣ ከምርት በኋላ በሚኖር ብክነትና በዝቅተኛ የምግብ ደኅንነት የሚፈተን መሆኑን በማመልከትም፣ በዝቅተኛ መጠን የሚያመርቱ አርሶ አደሮች እየተጎዱ እንደሚገኙና ለግብርና ሥራ ከፍተኛ ዋጋ ቢያወጡም፣ ትርፋቸው ዝቅተኛ መሆኑንም አንስቷል፡፡
እየጨመረ የመጣው የመሬት አቅርቦት ማነስና የሕዝቡ ቁጥር መጨመር ለእርሻ የሚውል መሬት በአማካይ ከነበረበት 0.65 ሔክታር እንዲቀንስ ማድረጉም፣ የመሬት ጥበቃንና ከተፈጥሮ ጋር ተስማሚ የሆነ ዘላቂ ምርታማነትን ለማስቀጠል ፈተና ደግኗል፡፡
በ2022 የነበረው ድርቅ በደቡብና ምሥራቅ ኢትዮጵያ አካባቢዎች፣ በተለይም አርብቶ አደሮችን ክፉኛ ጎድቷል፡፡ በአጠቃላይ በግጭትና በከፍተኛ ድርቅ ምክንያት ከቀዬአቸው የተፈናቀሉትን ጨምሮ 20 ሚሊዮን ሰዎች ለከባድ የምግብ ዋስትና ችግር መጋለጣቸውንም አሳይቷል፡፡
መቀንጨር፣ ከዕድሜ አንፃር ሊኖር የሚገባ ክብደት አለመመጣጠንና የሕፃናት ሞት ከዚህ ቀደም እየቀነሱ የነበረ ቢሆንም፣ በ2022 መጨመራቸው ሥር የሰደደ የምግብ ዋስትና ማጣትና የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ስለመኖሩ አመላካች ሆኗል፡፡
በኢትዮጵያ 6.8 በመቶ ከአምስት ዓመት በታች ያሉ ሕፃናት ሊኖራቸው ከሚገባው የክብደት መጠን በታች ናቸው፡፡ ይህም ላለፉት 15 ዓመታት ተመሳሳይ ሆኖ ዘልቋል፡፡ እንደ ሪፖርቱ ከሆነ ይህ ወደ አምስት በመቶ ዝቅ ማለት ነበረበት፡፡
የሕፃናት ሞት 4.9 በመቶ ሲሆን፣ ከ2000 ጀምሮ በግማሽ ቀንሷል፡፡ በተመድ የ2021 ሪፖርት መሠረትም፣ የጨቅላ ሕፃናት ሞት ከ1,000፣ 127 የነበረ ሲሆን፣ ከአምስት ዓመት በታች የሚከሰት ሞት ከ1,000፣ 47 ነበር፡፡ ከ20 ሕፃናት አንድ ልጅ አምስት ዓመት ሳይሞላውም ይሞታል፡፡
የሕፃናት መቀንጨር በጣም ከፍተኛ ሲሆን፣ መንግሥትም ይህንንና ተያያዥ ችግሮችን ለማቃለል የተለያዩ አሠራሮችን ቀይሶ ሲሠራ ከርሟል፡፡
በግብርና ሚኒስቴር የምግብና ሥርዓተ ምግብ ጽሕፈት ቤት አማካሪ ሙሉጌታ ተዓምር (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የምግብ አቅርቦትንና ተደራሽነትን ለማሟላት የተለያዩ ችግሮች አሉ፡፡ አንዱ ችግር የአየር ንብረት ለውጥ ሲሆን፣ ቶሎ ቶሎ የሚመጣ ድርቅ ችግሩን አባብሶታል፡፡
ከድርቅ በተጨማሪ አንዳንዴ የሚመጣው ዝናብ ከፍተኛ በመሆኑ የሚያስከትለው ጎርፍ ሌላው ችግር ነው፡፡ ግጭት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የማዳበሪያ መወደድና የዩክሬንና የሩሲያ ጦርነት ተደማምረው እስካሁን በግሎባል ሃንገር ኢንዴክስ ሪፖርት መሠረት ከዓመት ዓመት እየቀነሰ የነበረውን ረሃብ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እንዲጨምር አድርገዋል፡፡
የአየር ንብረት ለውጥ ረዥም ዓመታት ከማስቆጠሩ አንፃር፣ የዩክሬንና የሩሲያ ጦርነት ዓመት ያለፈው በመሆኑና ሌሎችም ዓመታት ያስቆጠሩ ችግሮችን ለመቅረፍ እንደ አገር ይህንን የሚቋቋም አሠራር አልተዘረጋም ወይ? የሚል ጥያቄ ያነሳንላቸው ሙሉጌታ (ዶ/ር)፣ ከዚህ ቀደም የተለያዩ ኢንሺየቲቮች እንደነበሩና ለረሃብ መቀነስ አስተዋጽኦ እንደነበራቸው አስታውሰዋል፡፡
ሆኖም እስካሁን የተሄደበት መንገድ የተበጣጠሰ ስለነበር ይህንን አቀናጅቶ ችግሩን ለመፍታት ኢትዮጵያ አካባቢን፣ የሰው ጤንነትን፣ የምግብ ተደራሽነትንና ተያያዥ ጉዳዮችን የሚያካትት የምግብ ሥርዓት ከሁለት ዓመታት በፊት አስተዋውቃለች ብለዋል፡፡
እንደ ሙሉጌታ (ዶ/ር)፣ የምግብ ሥርዓቱ 22 ውጤት ቀያሪ ነጥቦች አሉት፡፡ ምርት ሲመረት ከፍተኛ ውጤት ማግኘት ብቻ ሳይሆን አካባቢን መጠበቅ፣ የሚመረተው ምርት አቅም ላላቸው ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ዜጋ ተደራሽ እንዲሆን ማስቻልና በግብርና የተመጣጠነ ምግብ ተደራሽነትን ማጠናከር የሚሉትም ከነጥቦቹ ይገኙበታል፡፡
በ2030 ሁሉም ዜጋ ጤናማ የሆነ ምግብ እንዲያገኝ እየተሠራ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡
እንደ ሪፖርቱ፣ በ2022 በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ አሰቃቂ የሆነ መራብ ተመዝግቧል፡፡ በምግብ ሥርዓቱ ላይ ለተከሰተው ውድቀትም ተደራራቢ የሆኑ ዓለም አቀፍ ችግሮች አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
ረሃብ በደቡብ እስያ ቀዳሚ ሲሆን፣ አፍሪካ በተለይ ደቡብ ሰሃራ በሁለተኛ ደረጃ ይገኛል፡፡