በዓለም ላይ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተደራሽነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ይታመናል፡፡ በተለይ አዳዲስ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎች እንዲሁም መተግበሪያዎች ሲመጡ የአንድ አገር ኢኮኖሚያዊም ሆነ ማኅበራዊ ዕድገት ላይ ትልቅ ሚና እንዳለው መረጃው ያሳያል፡፡ የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለሥልጣንም በኢትዮጵያ ከ270 ሺሕ በላይ የቅጅ ወይም ኮፒ ራይትና መተግበሪያዎችን የሠሩ ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት መመዝገቡን አስታውቋል፡፡
የባለሥልጣኑ ሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ ኤልያስ መሐመድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የዜጎችን የፈጠራ ሥራዎቻቸውን በሕግ ከለላ ሥር እንዲሆንና ለፈጠራ እንዲነሳሱ ተቋሙ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ነው፡፡
በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ አቅም ዳብሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን ተቋሙ ያስቀመጠው የራሱ የሆነ ሕጎች እንዳሉት የገለጹት አቶ ኤልያስ፣ እነዚህንም ሕጎች ተፈጻሚ እንዲሆኑ በርካታ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ተቋሙም አራት ዘርፎች ላይ ትኩረት አድርጎ በመሥራት እየተንቀሳቀሰ ሲሆን፣ የማኅበረሰቡ ችግሮች የሚፈቱ ማሽነሪዎችና ሌሎች ቁሳቁሶች ተግባራዊ የሚያደርጉ ዜጎች የሚሰጥ መብት ፓተንት እንደሚባል አክለው ገልጸዋል፡፡
የአዕምሯዊ ንብረት ዘርፍ ሲሆን ይህም ዘርፍ በተቋሙ በኩል ተመዝግቦ ጥበቃ የሚያገኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በሌላ መልኩ የማኅበረሰቡ የዕውቀት ዘርፍ የተሰኘ አሠራርም በባለሥልጣኑ በኩል ተግባራዊ እንደሚደረግ፣ ይህም ባህላዊ ሕክምና፣ ባህላዊ መድኃኒቶችና በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ልዩ ጣዕም ያላቸው ምርቶች ጥበቃ የሚደረግላቸው መሆኑን ለሪፖርተር አብራርተዋል፡፡
እስካሁን ከ270 ሺሕ በላይ በኮፒራይትና መተግበሪያዎች ከ30 ሺሕ በላይ የውጭና የአገር ውስጥም የንግድ ምልክቶች መመዝገባቸውን ገልጸው፣ በፓተንት ደረጃ ደግሞ ከ890 ሺሕ በላይ ተመዝግበዋል ብለዋል፡፡
አብዛኛውን ተቋሞችም ሆኑ መተግበሪያን የሚሠሩ ግለሰቦች ወደ ተቋሙ መጥተው ምዝገባ ከማከናወን አንፃር ሰፊ ክፍተት እንዳለባቸውና የግንዛቤ ችግርም እንደሚታይባቸው አቶ ኤልያስ አብራርተዋል፡፡
በተለይ የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶች በማመሳሰል ወይም ደግሞ ኮፒ በማድረግ የተጠመዱ ተቋማሞች ሆኑ ግለሰቦች መኖራቸውን፣ እነዚህም ዜጎች ለሌሎች ሰዎች ሲሳይ መሆናቸውን አክለው ገልጸዋል፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ አብዛኛውን አገሮች በአኅጉራዊ ንብረት በኩል የሚፈጸሙ ሕጎች አክብረው እንደሚሠሩ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን ይህ ችግር እንዳለ ተናግረዋል፡፡
የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ተደራሽነት ከፍ ለማድረግ ተቋሙ የራሱ የሆነ አሠራር ዘርግቶ እየሠራ መሆኑን፣ በዘርፉ ያሉትን ችግሮች ለመቅረፍ ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ በቅርቡ እንኳን ‹‹ኑሀ የመንገድ ዳር መኪና ብልሽት›› ዕርዳታ ሰጪ የሞባይል መተግበሪያና ዲጂታል ‹‹ሳኮ ሲስተም›› የተባለ ወረቀት አልባ አሠራር የሚፈጥር እንዲሁም የብድርና የቁጠባ ተቋማት መረጃ አያያዝን ከመሠረቱ የሚቀይር መተግበሪያ ይፋ ተደርጓል፡፡