የመጀመሪያው አውሮፕላን በ1921 ዓ.ም. አዲስ አበባ መድረስ ለኢትዮጵያውን ከውጭው ዓለም ጋር ለመገናኘት አዲስ ዘመን የተከፈተበት ቀን መሆኑ አስደስቷቸዋል፡፡ ለፈረንሳዮቹ ደግሞ በኢትዮጵያ አቪዬሽን ታሪክ ከሌሎች አገሮች በተለይ ዝግጅቱን አጠናቆ ከነበረው ጀርመን መቅደማቸው አስደስቷቸዋል፡፡ ለአብዛኛው ኢትዮጵያ ግን የአውሮፕላን መምጣት ግርምትና ትእምረት ፈጥሮበታል፡፡ ያንን ለአዲስ ዘመን ቴክኖሎጂ ውጤት ማየቱ በአያሌው አስደንቆታል፡፡
‹‹ከቶ ምን አሳየኝ ይሠሩትን ያጡ
ጠንቀቅ በል ጌታዬ ወደ አንተም ጋር መጡ›› ብሎ እስኪዘምር ድረስ፡፡
መንገድ ሳይሠራለት፣ ሐዲድ ሳይነጠፍለት በአየር ላይ ተንሳፎ የመጣው ያን አውሮፕላን የአየር ባቡር የሚል ስም ወጣለት፡፡ ከዚያ ወዲህ አውሮፕላኑ ሁሉ የአየር ባቡር ሲባል POTE 2 ግን ርግበ ተፈሪ ተብሎ ተሰየመ፡፡
በዚህ ሁኔታ ነበር የዛሬ 85 ዓመት በኢትዮጵያ የአቪዬሽን ታሪክ የተጀመረው፡፡
ሁለተኛው አውሮፕላን የመጣው ደግሞ ነሐሴ 30 ቀን 1921 ነበር፡፡ የጀርመኑ ጀንከርስ (Junkers) አውሮፕላን በባሮን ሻን ኢግል አብራሪነት በከተማዋ ውስጥ ጃንሜዳ አረፈ፡፡ በጃንሜዳ ውስጥ በማረፉ ከፈረንሳዩ አውሮፕላን የበለጠ በርካታ ተመልካች እንዲኖር አድርጐታል፡፡ የፖስታ መልዕክትም ይዞ ስለነበረና ወዲያው እንዲታይ በመደረጉ ከቀድሞው በረራ የተለየ ተልዕኮ ያለው አደረገው፡፡ ንስረ ተፈሪ ተብሎ የተሰየመው ጀንከርስ አውሮፕላን በጃንሜዳ ሲያርፍ እንደበፊቱ ሁሉ የሞቀና የደመቀ አቀባበል ተደርጐለታል፡፡