በኢትዮጵያ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በሚዲያ ሙያዊ ድጋፍ ከሚያበረክቱ ጋዜጠኞች በዘለለ፣ በሙያቸው የበኩላቸውን ካበረከቱ አንጋፋ ባለሙያዎች መካከል አንደኛው ናቸው፡፡ በተለይ በአገር ውስጥ ስፖርታዊ ውድድሮች በፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት በቀዳሚነት ስማቸው ይጠቀሳል፡፡ በፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከተመረቁበት ጊዜ አንስቶ፣ በሙያቸው ለታሪክ የተቀመጡ በርካታ ምሥሎችን ማኖር ችለዋል፡፡
አቶ ብርሃነ በዛብህ ከአባታቸው ከአቶ በዛብህ አብተውና ከእናታቸው ከወ/ሮ የሹምነሽ ተፈሪ ግንቦት 6 ቀን 1948 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ሜክሲኮ ሠፈር ተወለዱ፡፡ ዕድሜያቸው ለትምህርት በደረሰ ጊዜ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርታቸውን በቀድሞ በየነ መርዕድ ትምህርት ቤት፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በቀድሞው ተፈሪ መኰንን ትምህርት ቤት እስከ 12ኛ ክፍል አጠናቀው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፎቶግራፍ ጋዜጠኝነት የትምህርት ክፍል መመረቃቸውን ከሕይወት ታሪካቸው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
አቶ ብርሃነ በተለይም ቤተሰቡ በሚታወቅበትና ከአባታቸው የስፖርት ጋዜጠኛው አቶ በዛብህ አብተው (ፎቶ በዛብህ) የወረሱትን የፎቶግራፍ ሙያ፣ በትምህርትና በቴክኖሎጂ በማዳበር በተለያዩ ስፖርት ነክና ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን ለታሪክ በማስቀመጥ ለትውልዱ መማሪያ እንዲሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
አቶ ብርሃነ በዛብህ በ1978 ዓ.ም በቀድሞ ስፖርት ኮሚሽን በመቀጠር፣ በተለያዩ ጊዜያት በተዘጋጁ አምስት የመላው አፍሪካ ጨዋታዎችና ኢትዮጵያ የተሳተፈችባቸው ታላላቅ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ መካፈል ችለዋል፡፡
ከዚያም በ2000 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ተቀጥረው እ.ኤ.አ. በ2004 በሲዲኒ፣ በ2008 በቤጂንግ፣ በ2012 በለንደን፣ በ2016 በሪዮ ኦሊምፒኮች ከኢትዮጵያ ልዑካን ጋር አብረው በመጓዝ ትልቅ አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ይህንንም ልምዳቸውን በመጠቀም የስፖርት ወዳጆች ሁሉ የተሟላ መረጃ ሊያገኙ የሚችሉበትን የኦሊምፒክ ሙዚየም በማደራጀት ታላቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
አቶ ብርሃነ ለአገራቸውና ለስፖርቱ ባላቸው ታላቅ ፍቅርና አክብሮት በሕመም በነበሩበት ወቅት እንኳን በሥራ ገበታቸው ላይ መቆየታቸው ወዳጆቻቸው ይመሰክራሉ፡፡
በዚህም በርካታ የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ የዕውቅና ሽልማቶችን ተበርክቶላቸዋል፡፡ ለአብነትም በቶሮንቶ ካናዳ፣ በዋሽንግተን ዲሲ፣ በሳንፍራንሲስኮ፣በሎስአንጀለስ፣ በዳላስና በአትላንታ በተደረጉት የሰሜን አሜሪካ የስፖርትና የባህል ውድድሮች ላይ ያገኟቸው የዕውቅና ሽልማቶች ተጠቃሽ ናቸው፡፡
አቶ ብርሃነ በዛብህ ቤተሰባቸውም ውስጥ ብዙ ትዝታ አላቸው፡፡ ቤተሰባቸውን ወዳጅና አርቆ አሳቢነታቸው፣ በተለይም በጨዋታ አዋቂነታቸው የቤተሰቡ ድምቀት እንደነበሩ ከሕይወት ታሪካቸው ላይ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
አቶ ብርሃነ ከባለቤታቸው ከወ/ሮ ሰላማዊት መስፍን ጋር ለ27 ዓመታት በፍቅር በፀና ትዳራቸው አንድ ወንድና አንድ ሴት ልጅም አፍርተዋል፡፡
አቶ ብርሃነ በዛብህ ባጋጠማቸው የጤና እክል ለረዥም ጊዜያት በአገር ውስጥና በውጭ አገር በሕክምና ሲረዱ ቆይተው፣ በተወለዱ በ67 ዓመታቸው መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡
ሥርዓተ ቀብራቸው መጋቢት 23 ቀን ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡