የመንግሥት የልማት ድርጅቶች የሕዝብ አገልግሎት እንዲሰጡ ግዴታዎችን የሚጥል ረቂቅ አዋጅ ለፓርላማ ቀረበ፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማክሰኞ መጋቢት 26 ቀን 2015 ዓ.ም. ባካሄደው 13ኛ መደበኛ ስብሰባ አዋጅ ቁጥር 25/1984ን የሚሽር የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቶ፣ ለዝርዝር ዕይታ ለመንግሥት የልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ መርቶታል፡፡
በረቂቁ እንደተመላከተው በገንዘብ ሚኒስቴር አማካይነት በሚቀርብ የመንግሥት ጥያቄ፣ ኢትዮጵያ ሆልዲንግስ ወይም አግባብ ያለው ተቆጣጣሪ ባለሥልጣን በመንግሥት ባለቤትነት የተያዘ የልማት ድርጅትን ከመመሥረቻ ጽሑፍ፣ ወይም ከማቋቋሚያ ደንቡ ጋር የሚጣጣም የሕዝብ አገልግሎት እንዲሰጥ ወይም እንዲያቆም በጽሑፍ ግዴታ ሊጥልበት ይችላል፡፡
በገንዘብ ሚኒስቴር የሚቀርበው የሕዝብ አገልግሎት ግዴታ ጥያቄ፣ የሕዝብ አገልግሎት ግዴታውን ለመወጣት በመንግሥት ባለቤትነት በተያዘው የልማት ድርጅት ላይ የሚያስከትለው ዓመታዊ አጠቃላይ ወጪ በግምት ያካተተ፣ የሕዝብ አገልግሎት ግዴታውን በመወጣት በመንግሥት ባለቤትነት ሥር ያለ የልማት ድርጅት የሚያገኘው ዓመታዊ ትርፍ ወይም የሚደርስበት ኪሳራ ግምት ውስጥ ያስገባ እንደሚሆን ተደንግጓል፡፡
በተጨማሪም የገንዘቡን ምንጭና የሕዝብ አገልግሎት ግዴታን ለመወጣት ከሚኒስቴሩ ወይም ከሌሎች ምንጮች የተገኘ ፈቃድ፣ በመንግሥት ባለቤትነት የተያዘው የልማት ድርጅት የሕዝብ አገልግሎት ግዴታውን በሚወጣበት ጊዜ እንዴት ቁጥጥር እንደሚደረግበት፣ አፈጻጸሙ እንደሚለካና የሕዝብ አገልግሎት ግዴታ አፈጻጸም ለሕዝብ ስለሚገለጽበት ዘዴዎች የሚኒስቴሩ ጥያቄ እንደሚካተት ተገልጿል፡፡
በረቂቅ አዋጁ ትርጉም ክፍል እንደተቀመጠው፣ የሕዝብ አገልግሎት ግዴታ ማለት፣ በአዋጁና በመንግሥት ባለቤትነት በተያዘው የልማት ድርጅት ማቋቋሚያ ደንብ ወይም ሚኒስቴሩ በሚያወጣው መመርያ መሠረት፣ በመንግሥት ባለቤትነት የተያዘ የልማት ድርጅት ዕቃዎችን ወይም አገልግሎቶችን ለሕዝብ ለማቅረብ የተጣለ ግዴታ ነው፡፡
በሌላ በኩል በመንግሥት ባለቤትነት የተያዙ የልማት ድርጅቶችን ወደ ግል ስለማዘዋወር በሚያብራራው የረቂቁ አንቀጽ 14፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ የሚያስተዳድራቸውን በመንግሥት ባለቤትነት የተያዙ የልማት ድርጅቶች በቦርዱ ፈቃድ ለመሸጥ መወሰን እንደሚችል ተብራርቷል፡፡
ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ወይም ከተቆጣጣሪ ባለሥልጣኑ በቅድሚያ የጽሑፍ ፈቃድ ካልተገኘ በስተቀር በመንግሥት የልማት ባለቤትነት የተያዙ ድርጅቶች ከአጠቃላይ ሀብቱ ከ50 በመቶ በላይ የሆነ ዕዳ ውስጥ መግባት፣ ተቀጥላ ድርጅትን የማቋቋም፣ በጋራ ኢንቨስትመንት መሳተፍ፣ ከኢትዮጵየ ውጪ ማናቸውም መጠን ያለው ኢንቨስትመንት ማድረግና ከኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ወይም ከተቆጣጣሪ ባለሥልጣኑ በቅድሚያ ፈቃድ ማግኘት የሚጠይቅ በሕግ የተመለከተ ማናቸውንም ነገር መፈጸም እንደማይችል በረቂቁ ተጠቁሟል፡፡