በኢትዮጵያ በጦርነቱ ምክንያት ከፍተኛ ጉዳት በደረሰባቸው ትግራይ፣ አማራና አፋር ክልሎች የሚገኙ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ አርሶና አርብቶ አደሮች፣ የተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችን ጨምሮ፣ ሌሎች የግብርና ግብዓቶች የሚያቀርብ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት በኩል ይተገበራል ለተባለው ለዚህ ፕሮጀክት፣ የአውሮፓ ኅብረትና የፈረንሣይ ልማት ኤጀንሲ በአጠቃላይ 32 ሚሊዮን ዩሮ ድጋፍ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡
ከአውሮፓ ኅብረት 14 ሚሊዮን ዩሮ፣ ቀሪው 18 ሚሊዮን ዩሮ ከፈረንሣይ ልማት ኤጀንሲ የተገኘለት ይህ ፕሮጀክት፣ በዋናነት በኢትዮጵያ በግጭት ውስጥ ለቆዩት ክልሎች የምግብ ዋስትና፣ እንዲሁም የተጎዳውን የግብርና እንቅስቃሴ መልሶ ለማሻሻል ዓላማ እንደሚውል ተገልጿል፡፡
የተገኘውን የገንዘብ ድጋፍ መሠረት በማድረግ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት በተለይም በሰሜኑ የአገሪቱ ከፍል በሚገኙትና በግጭት ውስጥ በቆዩት ትግራይ፣ አማራና አፋር ክልሎች ለሚገኙ አርሶ አደሮች ተፈላጊውን የግብርና ድጋፍ በማቅረብ እንደገና እንዲያመርቱ፣ ከዚህ ቀደም በገጠማቸው ከፍተኛ ቀውስ ምክንያት የተቋረጠውን የአገልግሎት መሠረተ ልማት ለማሻሻል የሚረዱ ድጋፎችን እንደሚያደርግ ተጠቅሷል፡፡
ፕሮጀክቱ ሁለት ዓይነት ጉዳዮችን ሲያካትት የመጀመሪያው በእነዚህ አካባቢዎች የግብርና ምርትን በማነቃቃት በጣም አስቸኳይ ፍላጎቶችን ማሟላት ሲሆን፣ የተቀረው የአርሶ አደሩ የምግብ ዋስትናን ማጠናከር ይሆናል ተብሏል፡፡
በፕሮጀክቱ የመጀመሪያው ምዕራፍ ከግማሽ ሚሊዮን ለሚበልጡ አባወራዎች የተሻሻሉ የእህል ዝርያዎች፣ የተሻሻሉ የዶሮ፣ የትንንሽ በግና ፍየል ዝርያዎች፣ የሆልቲካቸር ዝርያዎች፣ እንዲሁም ለመስኖ የሚያገለገሉ ፓምፖች ድጋፍ እንደሚደረግ መጋቢት 25 ቀን 2015 ዓ.ም. የአውሮፓ ኅብረትና የፈረንሣይ ልማት ኤጀንሲ የገንዘብ ድጋፍ ስምምነነቱን፣ በገንዘብ ሚኒስቴር የመሰብሰቢያ አዳራሽ በፈጸሙበት ሥነ ሥርዓት ተገልጿል፡፡
የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር)፣ ከሁለቱ የልማት አጋሮች በተገኘው ድጋፍ የሚተገበረው ፕሮጀክት በጦርነት በተጎዱ አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች የገጠሟቸውን የግብርና ምርቶች፣ የግብርና ምክርና ሙያዊ ድጋፍ፣ እንዲሁም ሌሎች ችግሮች እንዲቃሉላቸው ያደርጋል ብለዋል፡፡
በሰሜን ኢትዮጵያ ለሁለት ዓመታት የተደረገው ጦርነት ክፉኛ ከጎዳቸው ዘርፎች መካከል አንዱ የግብርና ዘርፉ መሆኑ፣ በተለይም በሰሜን የኢትዮጵያ ክፍል በርካታ የእርሻ መሬቶች ያለ ምርት እንዲከርሙ፣ የተዘራውም የሚሰበስበው ባለመኖሩ ረግፎ መቅረቱ ከዚህ ቀደም መገለጹ ይታወሳል፡፡
ለአብነትም በ2013/14 የምርት ዘመን በትግራይ ክልል 900 ሺሕ ሔክታር መሬት በዘር ሳይሸፈን እንደቀረ፣ በአማራ ክልልም በተመሳሳይ በዘር ተሸፍኖ ከነበረው 1.5 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በጦርነቱ ምክንያት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበት እንደነበር የግብርና ሚኒስቴር ማስታወቁ አይዘነጋም፡፡