- ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ
የካይሮ መልዕክቴ በዚሁ ብቻ አላበቃም። በ1950 ዓ.ም. ደግሞ በዚሁ ከተማ በተደረገው የመጀመሪያው የአፍሪካና የእስያ ሕዝቦች አንድነት ስብሰባ (አፍሮ ኤሺያን ፒፕልስ ሶሊዳሪቲ ኮንፈረንስ) ላይ ከሁለቱ አኅጉራት ማለትም ከአፍሪካና ከእስያ ከተላኩት መልክተኞች መካከል ከኢትዮጵያ ልዑካን አንዱ በመሆን የስብሰባው ተካፋይ ሁኜአለሁ።
ይህ ስብሰባ በግብጽ መንግሥት ጋባዥነት፣ በሕዝባዊ ድርጅቶች ወኪሎች ደረጃ የተደረገ ሲሆን፣ እኔ በስብሰባው ተካፋይ የሆንኩት ለኢትዮጵያ መንግሥት በደረሰው ጥሪ በአገሪቱ ከሚገኙ የምግባረ ሠናይ ድርጅቶች አንዱን፣ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በጎ አድራጎት ድርጅትን በመወከል ነበር። ሌሎቹ መልዕክተኞች ከኢትዮጵያ ሴቶች ማኅበር ወ/ሮ ሉሌ ተስፋዬ፣ አገር ፍቅር ማኅበር አቶ ጌታቸው መካሻ፣ ከመምህራን ማኅበር አቶ አበራ ሞልቶት፣ ከኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ልጅ ኃይሉ ደስታ፣ ከኢትዮጵያ የማዕድን ምርምር ተቋም አቶ ገብረ ክርስቶስ መርስዔ ሐዘን ነበሩ።
በጊዜው የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር በነበሩት በልጅ እንዳልካቸው መኮንን አማካይነት የልዑካን ቡድኑ ለስንብት በቀረብንበት ጊዜ ንጉሠ ነገሥቱ ‹‹የምትሄዱበት ጉባዔ ምን እንደሆነ ታውቁታላችሁ?›› ሲሉ ለጠየቁት ሁላችንም ተራ በተራ የመሰለንን መልስ ለመስጠት ሞከርን። የአንዳችንም መልስ አላረካቸውም። ልጅ እንዳልካቸውም ጣልቃ በመግባት የስጡትን መልስም አልተቀበሉም። በመጨረሻ “ጉባኤው በኮሚኒስቶች የተዘጋጀ መሆኑን አውቃችሁ በምታደርጉት ተካፋይነት ተገቢውን ጥንቃቄ ልታደርጉ ይገባችኋል›› ሲሉ አቅርበውልን ስለነበረውና እንቆቅልሽ ለሆነብን ጥያቄ ንጉሠ ነገሥቱ መልሱን ሰጡን። ጉዙአችን እንደዚህ ካለ ማስጠንቀቂያ ጋር ነበር፡፡ ካይሮ ደርሰን እንደተረዳነው ጉባዔው በእርግጥም በኮሚኒስት አገሮች የተዘጋጀ ዓላማውም በሁለቱ አኅጉራት ግንኙነት ብቻ የተወሰነ አልነበረም። በስንብቱ ጊዜ በቀረበልን ጥያቄ ብቻ ሳይሆን ከመካከላችን መሪው ማን እንደሆነ ስለአልተገለጸልን እንዴት እንደምናደርግ ተደናግረን ነበር። ካይሮ ከተያዘልን ሆቴል እንደደረስን ተሰብስበን ከተመካከርን በኋላ ከመካከላችን አንዲቱ ብቻ ሴት የሆኑትን ወ/ሮ ሉሌ ተስፋዬን መሪ፣ አቶ ጌታቸው መካሻን አፈ ጉባዔ (እስፖክስማን)፣ እኔ ደግሞ ጸሐፊ እንድሆን ልዑካኑ በስምምነት ስለመረጡ በጉባኤው መክፈቻ ላይ መሪዋ በአማርኛ የመልካም ምኞት መግለጫ እንዲያርጉና ትርጉሙን አቶ ጌታቸው በእንግሊዝኛ እንዲያሰሙ ተደረገ።
- አበራ ጀምበሬ ‹‹ድርሳነ ሕይወቴ››