ሦስተኛው የኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና ከመጋቢት 20 እስከ 24 ቀን 2015 ዓ.ም. ለተከታታይ አምስት ቀናት በኢትዮጵያ ስፖርት አካዴሚ ሲከናወን ቆይቷል፡፡ ውድድሩ የትራክና ሜዳ ተግባራት ዓይነቶችን አካቶ የማጣሪያና የፍፃሜ ውድድሮች አስተናግዷል፡፡
እምብዛም ትኩረት የማይሰጠውና የኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ ኮሚቴ ያዘጋጀው፣ የኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተቀዛቅዞ የነበረውን ውድድር ዳግም ለማነቃቃት ግብ አድርጎ እንደተሰናዳ ተገልጿል፡፡
ውድድሩን በይፋ የከፈቱት የኢትዮጵያ ፓራሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚዳንት ግዮን ሰይፉ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ የውድድሩ ዓላማ ተቀዛቅዞ የቆየውን የፓራሊምፒክ ስፖርት ለማነቃቃት ከመሆኑ ባሻገር፣ በቀጣይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለሚካሄዱ ውድድሮች ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶችን ለመምረጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡
በውድድሩ ከአምስት ክልሎችና ሁለት የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ሴቶች 126፣ ወንዶች 254፣ በአጠቃላይ 380 ስፖርተኞች፣ በተጨማሪም የኢትዮጵያ ስፖርት አካዴሚና የኦሮሚያ ኢንጂነሪንግ ኮንስትራክሽን ክለብ መሳተፋቸውን የብሔራዊ ፌዴሬሽኖች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቀልቤሳ ኤባ አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ በተለያዩ አገሮች በሚሰናዱ ውድድሮች ላይ፣ በተለይ በዓለም ሻምፒዮናና ኦሊምፒክ ላይ የሚወክሉ በርካታ አትሌቶች ባለቤት ናት፡፡ በአንፃሩ ኢትዮጵያ በፓራሊምፒክ መሳተፍ ከጀመረች ዘመናት ቢቆጠሩም፣ ለስፖርቱ ትኩረት መነፈጉ ይስተዋላል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1968 በእስራኤል ቴል አቪቭ በተካሄደው የበጋ ኦሊምፒክ ጨዋታ ጀምሮ መካፈል መጀመሯ ይነገራል፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያ ሁለት ስፖርተኞችን በጠረጴዛ ቴኒስና በአትሌቲክስ አሳትፋለች፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ኢትዮጵያ ለአሥር ዓመታት ከጨዋታው ርቃ ቆይታ፣ እ.ኤ.አ. በ1976 እንደገና መመለሷን አብርሃም ሀብቴ በሁለት ስፖርት መወዳደሩ ይታወሳል፡፡
ምንም እንኳ ኢትዮጵያ በፓራሊምፒክ መካፈል የጀመረችበት ጊዜ 60 ዓመት ቢሞላም፣ ለመጀመርያ ጊዜ ሜዳልያ ያሳካችው እ.ኤ.አ. በ2012 ለንደን ኦሊምፒክ ነበር፡፡ ወንድዬ ፍቅሬ በ1,500 ሜትር T-46 ውድድር የብር ሜዳሊያን ማሳካት የቻለ የመጀመርያው ኢትዮጵያዊ አትሌት ነበር፡፡ ሌላዋ ኢትዮጵያዊት ትዕግሥት መንግሥቱ በቶኪዮ ኦሊምፒክ በ1,500 ሜትር T-13 የወርቅ ሜዳሊያን ማሳካት የቻለች የመጀመሪያዋ ኢትዮጵያዊት መሆን ችላለች፡፡