ከሃያ ዓመታት በፊት የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ተወልደ ብርሃን ገብረእግዚአብሔር (ዶ/ር) ከቢቢሲ ሃርድ ቶክ አዘጋጅ ከቲም ሴባስቲያን ጋር ዘረመልን በተመለከተ ቃለ ምልልስ አድርገው ነበር፡፡ ስለ ዘርመል ምሕንድስና ሰጥተውት ከነበረ ምላሽ በወቅቱ በሪፖርተር የተስተናገደውን የተወሰነውን ክፍል እዚች ላይ ለአንክሮ ለተዘክሮ አቅርበነዋል፡፡
ቢቢሲ፡- ስለዘረመል ምግቦች ያለዎት አመለካከት ምንድነው?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- በዚህ በምሕንድስና ያልተመረተ በጣም የተትረፈረፈ ምርት አለ፡፡ በዚህ ዘዴ ያልተመረቱ ምግቦችን እነዚህ አገሮች ቀውስ በገጠማቸው ጊዜ መስጠት ከተቻለ፣ በዘረመል ምሕንድስና የተመረቱ ምግቦች ሊፈጥሩት የሚችሉትን ዘላቂ ችግር መቋቋም ይችላሉ፡፡ ሌሎች አገሮች ችግሩን መከላከል እንደተፈቀደላቸው፣ ልክ አውሮፓ እነዚህን ምግቦች ላለመቀበል እንደተፈቀደላት፡፡
ቢቢሲ፡- በአፍሪካ ያሉ አንዳንድ ሕዝቦች ግን በዘረመል ምሕንድስና የተመረቱ ምግቦች አይቀበሉም፡፡ እርስዎና እንደ እርስዎ ካሉ ሰዎች በሚሰጡዋቸው የማስጠንቀቂያ ምክንያት፣
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- አዎ፡፡
ቢቢሲ፡- እናም እርስዎም አስተዋጽኦ እያደረጉ ነው?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- የተመረዘ ምግብ ቢላክልን ዝም ብለን የምንቀበል ይመስልሃል?
ቢቢሲ፡- ይኼኮ የተመረዘ ምግብ አይደለም፣ በሚሊዮን የሚቆጠሩ አሜሪካውያን በየዕለቱ የሚመገቡት ነው፡፡
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- ልዩነቱን ለማስረዳት ዕድል ስጠኝ፡፡ በቢሊዮን የሚቆጠሩ አሜሪካውያን ይህንን የሚመገቡት አንዳንዴና ጥቂት ጥቂት ነው፡፡ ነገር ግን ለተራቡ ሰዎች ይህንን ምግብ በምትሰጥበት ጊዜ መቶ በመቶ ያ ነው የሚሆነው፡፡ በዘረመል ምሕንድስና የተመረተ የበቆሎ ወተትም ሊመጣ ይችላል፡፡ ሳይቀቀል ወደ አገር ውስጥ በማስገባቱ ሒደትም የሚመገቡት ገበሬዎች ሊያመርቱት እንደሚችሉ የታወቀ ነው፡፡ የቁጥጥር ሥርዓቱ በዚህ በዘረመል ምሕንድስና በተመረቱ በቆሎዎች ላይ ማተኮር አለበት፡፡
ቢቢሲ፡- በርካታ ሳይንቲስቶች ግንዛቤዎን ይቃወሙታል፡፡ በጆሃንስበርግ ተሰብስበው የነበሩ ሳይንቲስቶች ኬንያዊው ሳይንቲስት ባቀረቡት ረቂቅ ላይ ተወያይተው ነበር፡፡ መግለጫው እንደሚለው እነዚህን በጄኔቲክ ቴክኖሎጂ የተመረቱ ምግቦች አንዳንድ የአፍሪካ አገሮች አለመቀበላቸው በሳይንሳዊ መረጃ ላይ የተመሠረተ አይደለም፡፡ እንደ አፍሪካዊው ሳይንቲስት እነዚህን ምግቦች ማገድ ሥነ ምግባር የጎደለው (Unethical) እና ኢሰብዓዊ ነው፡፡ በዘረመል ምግቦች ሰበብ የብዙ ሰዎችን ሕይወት ፖለቲካዊ ጨዋታ ውስጥ በመጣል የታቀዱ ናቸው፡፡
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- ሁሉም አፍሪካውያን ሳይንቲስቶች የሚሉት ነው? ከሆነ የእኔም ሐሳብ ይሆናል፡፡ በዘረመል ምሕንድስና ያልተመረቱ ሰብሎች በሚገኙ ጊዜ የአፍሪካ አገሮች የየራሳቸውን የቁጥጥር ሥርዓት ለመዘርጋት ዕድል ያገኛሉ፡፡ በዘረመል ምሕንድስና የተመረቱ ሰብሎችን በተመለከተም ለማስተዋወቅም ይሁን ላለማስተዋወቅ ውሳኔ ለመስጠት ጊዜ ያገኛሉ፡፡ ከዚህ አደጋ ራስን አለመጠበቅ ትልቅ ወንጀል ነው፡፡ አንድም ከተቻለ ዛሬ በዚህ ዘዴ እየተመረተ ያለው ምግብ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚመረተው ዘረመልዕ ያልሆነ ምርት አንፃር በጣም ጥቂት ክፍልፋይ ነው፡፡ በዩናይትድ ስቴትስ እንኳ በዚህ ምሕንድስና ያልተመረቱ በጣም ብዙ ምግቦች አሉ፡፡ ለምሳሌ ምንም ዓይነት ስንዴ በዘረመልእ ምሕንድስና አልተመረተም፡፡
ቢቢሲ፡- በዘረመል ምሕንድስና የተመረቱ ምግቦችን ከመብላት መራብና መሞት ይሻላል?
ተወልደብርሃን፡- ይህ ጥያቄ ቅድም እንደነገርኩህ ከባድ ነው፡፡ በቀላሉ ሊመለስ የማይችል ጥያቄ ነው፡፡ ከምግብ ሌላ ምንም ዓይነት አማራጭ የሌላቸው ይመስላል፡፡ አመራጮች አሉ ግን በሁኔታው ከማስገደድ ለምን ሌሎች አማራጮችን አንፈልግም?
ቢቢሲ፡- ያ በዘረመል ምሕንድስና የተመረተ ምግብ ነው ጉዳት የሚያመጣው?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- ሐሳቤን መግለጽ አለብኝ፡፡ ራሴን እንጂ እነሱን አልወክልም፡፡ ለማውቀው ነገር እኔ ራሲ ሳይንቲስት ነኝ፡፡
ቢቢሲ፡- ይህ አፍሪካን እንደማገት ነው?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- አፍሪካን በታጋችነት መያዝ ስትል ምን ማለትህ ነው?
ቢቢሲ፡- የእርሻ ኩባንያዎች በእነርሱ ጥራጥሬዎች ላይ ጥገኛ ሊያደርጉን ይህንን ፓተንት እየተጠቀሙበት ነው፣ እናም እነዚህን በዘረመል ምሕንድስና የተመረቱ ዝርያዎችን ከመጠቀም የከፋ ቅኝ ግዛት የለም፡፡
ተወልደብርሃን፡- በትክክል፣
ቢቢሲ፡- ይህንኑ ነው እያሉት ያለው?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- አዎ፡፡ እናንተ አስቀድማችሁ ታውቁታላችሁ… አሁን ይኼ የተለየ በቆሎ፡፡ አፍሪካ የሄድክ እንደሆነ አንዳንድ ገበሬዎች ይዘሩታል፡፡ በነፋስ ተሸካሚነት በመሠራጨት ያልተዘራውም ያው ዓይነት ይሆናል፡፡ እንግዲህ ሁሉም የበቆሎ ዘር በእነዚህ ኩባንያዎች ሀብትነት የተመዘገበውን ሆነ ነው ማለት የዓለም ንግድ ድርጅት የፈጠራ መብት ማስጠበቂያ አንቀጽ 34 ይህንን ዓይነት ዘር የገበሬዎች አይደለም ነው የሚለው፡፡
ቢቢሲ፡- መሟገት ይቻላል፡፡ ደግሞም ተሟግተው የረቱ አሉ?
ተወልደ ብርሃን፡- ለመሟገት ያንን ያህል ገንዘብ የት አግኝተው?
ቢቢሲ፡- ይቻላል ከብሔራዊ መንግሥታት…
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- አይደለም ይኼ ነገሩን ያለ ቅጥ አቅልሎ ማየት ይሆናል፡፡
ቢቢሲ፡- ለምሳሌ ደቡብ አፍሪካ ተከራክራ አሸንፋለች፡፡
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- እኔ እየተናገርኩ ያለሁት ራሳቸውን ችለው ኒውዮርክ ፍርድ ቤት ሄደው ክስ መመሥረት ስለማይችሉ ገበሬዎች ነው፡፡
ቢቢሲ፡- ምዕራባውያን ምን ያድርጉ ታዲያ?
ተወልደ ብርሃን (ዶ/ር)፡- ምዕራባውያን ፍትሐዊ ንግድ እንዲኖር የምትፈልጉ ከሆነ ልዘርዝርልህ፡፡ ለግብርና የሚደረገውን ድጎማ ማቆም፣ ለአፍሪካ ምርቶች ገበያዎቻችሁን ክፍት አድርጉ ይህንንም ለማድረግ የመዋቅር ማስተካከያ አድርጉ…