የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩትና ጤና ሚኒስቴር ከተባባሪ አካላት ጋር ያከናወኑት የምግብና ሥርዓተ ምግብ ስትራቴጂ መነሻ ዳሰሳ ጥናት፣ የምግብና ሥርዓተ ምግብ አለመሟላት የኢትዮጵያ አሳሳቢ የልማት ሥጋት መሆናቸውን አመላክቷል፡፡
መጋቢት 14 ቀን 2015 ዓ.ም. ይፋ የተደረገውን የዳሰሳ ጥናት አስመልክቶ ጤና ሚኒስቴር በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ጥናቱ በሁሉም ክልሎች ዝቅተኛ የምርት ስብጥር መኖሩ ያሳየ ሲሆን፣ የሕፃናት የመቀንጨር ምጣኔም እ.ኤ.አ. በ2016 ከነበረው ብዙም ለውጥ አላሳየም፡፡
ዳሰሳው እንደሚያመለክተው፣ የሕፃናት መቀንጨር አሁንም የኢትዮጵያ ዋና የኅብረተሰብ ጤና ችግር ሆኖ ቀጥሏል፡፡ ከአምስት ዓመት በታች ከሚገኙ ሕፃናትም 39 በመቶው መቀንጨራቸውን (በዕድሜያቸው ልክ ሊኖር ከሚገባ ቁመት በታች መሆናቸውን) አሳይቷል፡፡
11 በመቶ የሚሆኑ ከአምስት ዓመት በታች ያሉ ሕፃናት ካላቸው ቁመት ጋር የሚመጣጠን ክብደት እንደሌላቸው፣ 22 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ በዕድሜያቸው ሊኖራቸው የሚገባውን ያህል ክብደት እንደሌላቸው በጥናቱ ተስተውሏል፡፡
ስድስት በመቶ ሕፃናትም በዕድሜያቸው ሊኖራቸው ከሚገባ ክብደት በላይ አስመዝግበዋል፡፡
በ2016 ከተደረገው ጥናት አንፃር በአንዳንድ ጠቋሚዎች መሻሻል የታየ ቢሆንም፣ በጥናቱ በሁሉም ክልሎች ከፍተኛ የማይክሮኒውትረንት (የንጥረ ምግቦች እጥረት) በስፋት መኖሩ ታይቷል፡፡
በሁሉም ክልሎች ከግማሽ በላይ የሚሆኑ ለአካለ መጠን የደረሱ ሴቶች፣ በወጣትነትና በጉርምስና ዕድሜ ላይ ያሉ ልጃገረዶችና ሕፃናት የንጥረ ምግቦች እጥረት ተጎጂ መሆናቸውም በዳሰሳ ጥናቱ ተመልክቷል፡፡
ትንሽ መሻሻል ቢኖርም፣ በኢትዮጵያ ከአምስት ዓመት በታች የሚገኙ ሕፃናት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት አሁንም ከፍተኛ ነው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ ከአምስት ዓመት በታች ከሚገኙ ሕፃናት ግማሽ ያህሉ በተለያየ ዓይነት የተመጣጠነ ምግብ እጥረት የተጎዱ ናቸው፡፡ የቀነጨሩ ሕፃናት ምጣኔም የገጠሩ ከከተማ ሲነፃፀር፣ የገጠሩ 43 በመቶ በመሆን ከፍተኛ ሲሆን፣ በከተማ 29 በመቶ ነው፡፡
ከዕድሜ አንፃር ከሚፈለገው ክብደት በታች መሆንም፣ በገጠራማ አካባቢዎች 12 በመቶ ሲሆን፣ በከተማ ስምንት በመቶ ነው፡፡ የተመጣጠነ ምግብ አለማግኘት በኢትዮጵያ በተለያዩ ክልሎች የተለያየ ምጣኔ ያለው ሲሆን፣ የዚህ አመላካች የሆነው መቀንጨር በአፋር 42 በመቶ፣ በኦሮሚያ 41 በመቶ፣ በአማራ 40 በመቶ፣ በደቡብ 40 በመቶ መሆኑም በዳሰሳው ተመልክቷል፡፡
ለአቅመ አዳም ከደረሱ ሴቶች 19 በመቶ ያህሉ ከክብደት በታች መሆናቸውን የጠቆመው ጥናቱ፣ ከእነዚህም 22 በመቶ በገጠር እንዲሁም 15 በመቶ በከተማ አካባቢዎች የሚኖሩ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
እንደ ዳሰሳ ጥናቱ፣ ከስድስት እስከ 23 ወራት ካሉ ሕፃናት 47 በመቶ ያህሉ ከፍተኛ የምግብ እጥረት (የምግብ ድህነት) አለባቸው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ 75 በመቶ በሶማሌ፣ 53 በመቶ በደቡብ፣ 50 በመቶ በጋምቤላ የሚገኙ ናቸው፡፡ በዚሁ የዕድሜ ክልል ውስጥ ካሉት ሕፃናት 45 በመቶ ያህሉ መካከለኛ የምግብ እጥረት ያለባቸው ናቸው፡፡
በዳሰሳው ከታዩ አንኳር ጉዳዮች አንዱ ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ ነው፡፡ ጤናማ ያልሆነ የምግብ አጠቃቀምን በተመለከተ ከስድስት እስከ 23 ወራት ካሉ ሕፃናት 15 በመቶው ጤናማ ያልሆነ አመጋገብ እንዳላቸው ተመልክቷል፡፡
ከእነዚህ ከፍተኛውን ድርሻ በመያዝ አዲስ አበባ 35 በመቶና ሲዳማ 31 በመቶ ሲመዘገብ፣ አፋር ሁለት በመቶ፣ ድሬዳዋ ስምንት በመቶ እንደሁም ሶማሌ ዘጠኝ በመቶ በመሆን ዝቅተኛውን ሥፍራ ይይዛሉ፡፡ ጤናማ ያልሆነ ምግብ ከሚመገቡ ታዳጊ ልጆች 23 በመቶው በከተሞች አካባቢ የሚኖሩ ሲሆን፣ 12 በመቶው በገጠራማ አካባቢ የሚኖሩ ናቸው፡፡
69 በመቶ ያህል ከስድስት እስከ 23 ወራት ያሉ የአዲስ አበባ ሕፃናት ከፍተኛ ጣፋጭ መጠጦች (ከአልኮል ነፃ) የሚጠቀሙ ሲሆን፣ በዚሁ የዕድሜ ክልል የጣፋጭ መጠጦች አጠቃቀም በከተሞች ከፍተኛውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ በከተሞች ከሁለት ሕፃናት አንዱ የጣፋጭ መጠጥ ተጠቃሚ ሲሆን፣ በገጠራማ አካባቢዎች ከአራት ሕፃናት አንዱ ብቻ ይጠቀማል፡፡
እንደ ዳሰሳ ጥናቱ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ አጠቃቀም በብሔራዊ ደረጃ ሲታይ ዝቅተኛ ነው፡፡ ከስድስት እስከ 23 ወራት ካሉ ሕፃናት ውስጥ ከአራቱ ሦስቱ አትክልትና ፍራፍሬ አልተመገቡም፡፡ ምጣኔው ደግሞ በክልሎች ላይ ያይላል፡፡
እነዚህንና በክፍት ቦታ መፀዳዳት፣ ጡት ማጥባት፣ የግብርና መሬት ለምነትና አስተዳደር፣ በአዮዲን የበለፀገ ጨው፣ የሴፍቲኔት ፕሮግራም ሽፋን፣ የተሻሻለ የውኃ አቅርቦትና የሴቶች አቅም ግንባታን ጨምሮ የተሠራው ዳሰሳ፣ በአጠቃላይ ያመለከተው የሕፃናትና የእናቶችን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ለመቀነስ የተወሰዱ ዕርምጃዎች ውስን ዕድገት ማስመዝገባቸውን ነው፡፡
ውስን ዕድገት እንዲመዘገብ ደግሞ፣ የኮቪድ 19 ወረርሽን፣ የምግብ ዋጋ መናር፣ የበረሃ አንበጣ፣ የአዝርዕ ምርት አለመስጠት፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሰብዓዊ ድጋፍ አለመመጣጠን በሁሉም ደረጃ በዘርፉ የሚሠሩ አካላት የአተገባበር ችግር መኖር እንደ ምክንያት ተቀምጧል፡፡
የዳሰሳ ጥናቱ ምግብና ሥርዓተ ምግብ ላይ የታዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ሊወሰዱ ይገባል ብሎ ካሰፈራቸው ሐሳቦች፣ በሁሉም ደረጃ ያሉ ትብብሮችን ማጠናከር፣ ባለቤትነትና ተጠያቂነትን ማስፈን፣ ከመንግሥት፣ ከጋር ድርጅቶችና ከግሉ ዘርፍ ተጨማሪ ገንዘብ ማሰባሰብ፣ የምግብና የተመጣጠነ ምግብ መረጃ ሥርዓት መዘርጋትና እንደ የሌማት ትሩፋትና የአረንጓዴ አሻራ ዓይነት ኢንሽየቲቮችን ማበረታታት የሚሉት ይገኙበታል፡፡
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ደ/ር) እንዳሉት፣ መንግሥት እ.ኤ.አ. በ2018 የምግብና ስርዓተ ምግብ ፖሊሲን ያጸደቀ ሲሆን፣ የ10 ዓመት ብሄራዊ የምግብ እና ስርዓተ ምግብ ስትራቴጂ ፀድቆ ፈፃሚ ሴክተሮች እየተገበሩት ይገኛል፡፡
ለአብነትም በሁሉም ክልሎች በሚገኙ በ240 ወረዳዎች እየተተገበረ የሚገኘውን የሰቆጣ ቃልኪዳን እና በቅርቡ የተጀመረውን የሌማት ትሩፋትም ጠቅሰዋል።
በኢትዮጵያ ባለፉት አመታት በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ሆኖም የስርዓተ ምግብ ችግር አሁንም ከፍተኛ ትኩረት የሚሻ ሀገራዊ አጀንዳ መሆኑን፣ የምግብና ስርዓተ ምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ሰፊ ርብርብ እንደሚጠይቅና የዳሰሳ ጥናቱም ይህን እንዳረጋገጠ ሊያ (ዶ/ር) ገልፀዋል።
በሴቶች፣ ከአምስት ዓመት በታች ባሉ ህፃናት፣ እድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ህጻናት እና ወጣቶች ላይ ያለውን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ለመገንዘብ፤ በስነ-ምግብ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያሉ ክፍተቶችን ለመለየት እና የማይክሮኒውትረንት (ለሰውነት በጥቂት መጠን የሚያስፈልጉ ልሂቅ ንጥረ ነገሮች) እንዲሁም የግብርና የአፈር ንጥረ ነገሮችን ሁኔታ ለመወሰን የሚያስችሉ ግብአቶችን ለማግኘት ዓላማ አድርጎ በተሰራው የዳሰሳ ጥናት፣ ከ16,000 በላይ ቤተሰቦችና የብሄራዊና የክልል ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡
ለጥናቱ ከ2 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ እንደተደረገም የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በማህበራዊ ትስስር ገጹ አስፍሯል፡፡