አየርላንድ እጅግ ከፍ ባለ ሁኔታ የምታከብረው የቅዱስ ፓትሪክ ቀን በሚውልበት መጋቢት 8 (እ.ኤ.አ. ማርች 17) ቀን የአየርላንድ ህዝብ፣ ዲያስፖራው እና በዓለም ዙሪያ ያሉ የአየርላድ ወዳጆች በአጠቃላይ በአየርላንድ ታሪክ ውስጥ ወሳኝ የሆኑ ኩነቶች አንድ ላይ የሚገጥሙበትን ልዩ ክስተቶች በጉጉት እየተጠባበቁ ይገኛሉ። ይኽን የዘንድሮውን አመት በታሪክ ውስጥ መለስ ብለን ስንመለከት፣ አየርላንድ የመንግስታቱን ማህበር ወይም ሊግ ኦፍ ኔሽንስ በአባልነት ከተቀላቀለች 100 አመት የሚሆንበት፣ አገሪቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ከሆነች 50 አመት የሚደፍንበት፣ እንዲሁም ደግሞ በሰሜን አየርላንድ ሰላምን እንዲሰፍን ያስቻለው ታሪካዊው የጉድ ፍራይዴ ስምምነት የተፈረመበት 25ኛው አመት የሚታሰብበት ነው።
በምዕራባዊው አውሮፓ እንደምትገኝ አንድ ትንሽ አገር፣ አየርላንድ ከአቅራቢያ አገራት አልፎ በርቀትም ከሚገኙት ጋር ጠንካራ የሆኑ የባህል፣ የኢኮኖሚ እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቶች መኖርን ወሳኝነትና አስፈላጊነት በጥልቀት ትገነዘባለች። በአውሮፓዊያኑ ‘የጨለማ ዘመናት’፣ የአየርላንድ መነኮሳት እና ምሁራን ክርስትናን ለመስበክ፣ እንዲሁም ደግሞ ለትምህርት እና የተሳሰረች አውሮፓን ለመፍጠር ሃሳብ ራሳቸውን መስዋዕት በማድረግ እጅግ አስችጋሪ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ ራቅ ወዳሉ ስፍራዎች ይጓዙ ነበር። በ 19ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ተከስቶ የነበረውና ከፍተኛ እልቂት ያስከተለው የረሃብ አደጋ አየርላንድ ከተቀረው ዓለም ጋር የነበራትን ግንኙነት በጉልህ የሚያሳይ ነው። በጊዜው የኦቶማኑ ሱልጣን እና ቾክቱ በመባል የሚጠሩት ቀደምት (ኔቲቭ) አሜሪካዊያን የዕርዳታ ጥቅሎችን ለአየርላንድ ልከው ነበር፤ በቁጥር ወደ 2 ሚሊዮን ይደርሱ የነበሩ አየርላንዳዊያን ከደረሰባቸው መከራ ለመሸሽ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ አገራት ተሰደው ነበር። እነዚህ አለም አቀፋዊ ትስስሮች አየርላንድ ከአንድ አመት ቀደም ብሎ ከዩናይትድ ኪንግደም ነጻነቷን መቀዳጀቷን ተከትሎ ማለትም በ 1915 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. 1923) ጣልያን በ 1928 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. 1936) ኢትዮጵያን በወረራ መያዟን በመቃወም ለኢትዮጵያ ሏአላዊነት መጠበቅ ያላትን ጠንካራ ድጋፍ ያሳየችበትን የመንግታቱን ማህበር በአባልነት በመቀላቀል በአለም መድረክ ላይ የሚገባትን ስፍራ ስትይዝ ይበልጥ ጠንካራ መሰረት ለመያዝ ችለዋል።
ያ ወሳኝ መቶ ክፍለ ዘመን በያዝነው አመት አየርላንድ ታህሳስ 23 ቀን 1965 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. ጃንዋሪ 1 ቀን 1973) የአውሮፓ ህብረትን በአባልነት የተቀላቀለችበትን 50ኛ አመት ከምታከብርበት ወቅት ጋር መጋጠሙ ምልኡ እንዲሆን አድርጎታል። ይኽ የታሪክ ኩነት ለአየርላድ ወደ አንድ የዳበረች ሉዓላዊ አገርነት ሽግግር በጣም ወሳኝ ከመሆኑም ባሻገር እነዚህ 50 አመታት አገሪቱ ከኋላቀርነትና ከግብርና ኢኮኖሚ ወደ አገልግሎት – መር እና በከፍተኛ ደረጃም ኢንዱስትሪያዊ ማህበረሰብነት ላደረገችው ሽግግር ምስክሮች ናቸው። እንደ አንድ ኩሩ አውሮፓዊ አገር ያደረግነው ጉዞ አየርላንድ ከአህጉራዊ አጋሮቻችን ጋር ብቻ ሳይሆን በመላው አፍሪካ እና ከዓለም ደቡባዊ አገራት ጋር ይበልጥ መዋሃዳችንን ያሳየ ነው። ወደ ልማት ባደረግነው ጉዞ በጽናት የተቋቋምናቸውን መከራዎች የአየርላንድ ህዝብ ፈጽሞ አይረሳቸውም፤ የአየርላንድን ወደ አውሮፓ ህብረት መቀላቀልን በቅርበት ተከትሎ የአየርላንድ መንግስት የአለም አቀፍ ልማት ፖሊሲና ፕሮግራም (አይሪሽ ኤድ) በ 1966 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. 1974) መቋቋሙም የአጋጣሚ ጉዳይ አይደለም። ከዛ ጊዜ አንስቶም፣ አየርላንድ በቁጥር 130 ለሚሆኑ አገራት በቢሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር የልማትና የሰብዓዊ እርዳታ በመስጠት ድጋፍ አድርጋለች፤ ኢትዮጵያም የሁለትዮሽ እርዳታ ድጋፉ ትልቋ ተቀባይ አገር ነች።
እ.ኤ.አ. የ 1970ዎቹ የመጀመሪያ አመታት በአየርላንድ ታሪክ ውስጥ ለየት ባለ ሁኔታ እንዲታዩ የሚያደርጋቸው ሌላም ምክንያት አለ። አሁንም ድረስ የዩናይትድ ኪንግደም አካል የሆነውና የአየርላድ ደሴት አንድ ክፍል የሆነው ሰሜናዊ አየርላንድ እንዲሁም አየርላንድ ውስጥ ለ 50 አመታት የከፋ ሁከትን ያስከተለ በአንጃ የተከፋፈሉ ወገኖች መካከል ግጭት የተካሄደበት ‘የችግሮች’ ወቅት መሆኑ ነው። ይኽ ለ 30 አመታት ያህል የቆየው አስከፊ ግጭት ሁከትን ብሎም በደሴታችን
ማህበረሰቦች ውስጥ መከፋፈልን አስከትሏል። ይኽ ግጭት በ 1990 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. 1998) በጉድ ፍራይዴ የሰላም ስምምነት መቋጫውን ካገኘ ወዲህም ህይወት በደሴቲቷ ከብጥብጥና ከሁከት ወደ ሰላማዊነት ተቀይራለች። ልክ እንደ ሌሎቹ የሰላም ስምምነቶች ሁሉ ይኽም ስምምነት ፍጹም አይደለም፤ ሆኖም ግን በአየርላንድ እና በሰሜናዊ አየርላንድ እጅግ የብዙሃኑን ተቀባይነት ያገኘ ከመሆኑም በላይ ግጭቱ እንዲያበቃ አድርጓል። ከሩብ መቶ ክፍለ ዘመን በኋላም በስምምነቱ የተጀመረው የሰላም ሂደት እንደቀጠለ ነው። እርቅ የማውረዱ አስቸጋሪ ስራ አመታትን የሚወስድ ቢሆንም ቅሉ፣ በስንት ጥረት የተገኘ ሰላም ግን ከየትኛውም አማራጭ የተሻለ ነው።
አየርላንድ እነዚህን ሶስት ክብረ በዓላት መለስ ብላ በምትቃኝበት የቅዱስ ፓትሪክ መታሰቢያ ዕለት እንዲሁም እንደ ነፃ አገርም አንድ ክፍለ ዘመን በደፈንበት በዚህ ወቅት፣ ህዝባችን በጉዟችን ያጋጠሙንን መከራዎች እና የሃሴት ጊዜያት በእኩል ሁኔታ ለመመዘን እንዲሁም ደግሞ መሪነትን ለማሳየትና ሁላችንም ለተጋፈጥናቸው ዓለም አቀፋዊ ተግዳሮቶች የበኩሉን መፍትሄ ለማበርከት ቁርጠኛ ነው። እኛ አየርላንዳዊያን በቋንቋችን አንድ አባባል አለን – ያለ አንድነት ምንም አይነት ጥንካሬ የለም! እርስ በርሱ እንደተጋመደ አለም በጋር ስንቆምም የበለጠ እንጠነክራለን፤ ይኽን ለማሰላሰልም የቅዱስ ፓትሪክ መታሰቢያ ዕለት ወሳኙ ወቅት ነው።