በኢትዮጵያ ውስጥ ለረዥም ዓመታት የቤተሰብ ንግድን አስቀጥለው የሚገኙ ተቋማት ያሉባቸውን ችግሮች ለመፈተሽና ‹‹በዘርፉ ላይ እንዴት ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ አለባቸው?›› የሚለውን ለመለየት ጥናት ሊያካሂድ መሆኑን ኤችኤስቲ ኮንሰልቲንግ ኃላፊነነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር አስታወቀ፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የቤተሰብ የንግድ ተቋማቶች ቀጣይነታቸው በምን ላይ ይገኛል? የሚለውን ለመለየትና የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ተቋሙ መጋቢት 1 ቀን 2015 ዓ.ም. ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
የማኅበሩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ግዛው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የንግድ ተቋማት ካደጉት አገሮች ተሞክሮ ወስደው ቀጣይነት ያለው የንግድ ሥርዓት እንዲዘረጉ፣ እንዲሁም በቀጥታም ሆነ በተዘዋወሪ የአገሪቱ ኢኮኖሚን አንድ ዕርምጃ ከፍ እንዲያደርጉ ማኅበሩ ጉልህ ድርሻ ይወጣል፡፡
በኢትዮጵያ አብዛኛውን የቤተሰብ የንግድ ተቋማት ከአመራር ክፍተት፣ ተወዳዳሪ ሆኖ ከመቀጠል ይልቅ በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ከንግድ ሥርዓቱ እንደሚወጡ፣ በዚህም የተነሳ በዘርፉ ላይ ከፍተኛ የሆነ ክፍተት መፈጠሩን አቶ ሰለሞን አስረድተዋል፡፡
በተለይም በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚገኙ ተቋማት አብዛኛዎቹ ከቤተሰብ ቢዝነስ ጎራ የሚመደቡና ለረዥም ዓመታት በዘርፉ ላይ በመቆየት ምርቶቻቸውን ያለማቋረጥ በማሻሻልና ተወዳዳሪነታቸውን በማረጋገጥ፣ የአገራቸውን የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አሻራቸውን መጣል የቻሉ መሆናቸውን አክለው ገልጸዋል፡፡
በዚህ መሠረት በኢትዮጵያ የሚገኙ ተቋማት ራሳቸውን በማሻሻልና የአገራቸውን የኢኮኖሚ ዕድገት አንድ ዕርምጃ ከፍ በማድረግ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ መወጣት እንዳለባቸው፣ ይህም ተፈጻሚ እንዲሆን ማኅበሩ 400 ተቋማት ላይ ጥናት ለማድረግ ቅድመ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አብራርተዋል፡፡
ጥናቱም የሚደረገው ለስድስት ወራት ያህል መሆኑን፣ በቀጣይ ተመሳሳይ በሆነ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ጽሐፎችን በማዘጋጀት ከተቋሞች ጋር የምክክር መድረክ እንደሚዘጋጅ ዋና ሥራ አስፈጻሚው ለሪፖተር ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ አብዛኛዎቹ የቤተሰብ የንግድ ተቋማት እንደ ጊዜው ቀልጣፋና ዘመናዊነት አሠራርን ባለመከተላቸው የተነሳ ተቋማቱ ሲዘጉ አሊያም ደግሞ በሌላ ወገን ሲመሩ ይታያል ያሉት የኅብረት ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መላኩ ከበደ ናቸው፡፡
በአሁኑ ወቅት የቤተሰብ የንግድ ተቋማት ከትውልድ ወደ ትውልድ የንግድ ሥርዓታቸውን እንዲያስቀጥሉ፣ እንዲሁም ያለባቸውን አቅም እንዲያሳድጉ ወጥ የሆነ ሥራ መሥራት እንዳለበት አቶ መላኩ ገልጸዋል፡፡
በቀጣይ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚታዩ የቤተሰብ ቢዝነሶች ያሉባቸውን ተግዳሮቶችና የወደፊት መፍትሔዎች ላይ የሚያተኩር ውይይት ሰኔ ወር የሚካሄድ መሆኑ ተገልጿል፡፡