በኢትዮጵያ የሚኖሩ አብዛኛው ሴቶች በተለያዩ ምክንያቶች ‹‹የበይነ መረብ አጠቃቀማቸው ዝቅተኛ መሆኑ፣ ኑሮዋቸውን ለማሻሻል የሚያደርጉትን ጥረት ወደኋላ እንደጎተተው የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሪት ፍሬሕይወት ታምሩ ገለጹ፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም የዓለም የሴቶች ቀንን አስመልክቶ፣ ‹‹የዲጂታል አገልግሎት ለሥርዓተ ጾታ እኩልነት›› በሚል መሪ ቃል፣ የካቲት 29 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ የጽዳት አገልግሎት ከሚሰጡ ሴት ሠራተኞች ጋር አክብሯል፡፡
‹‹ሴቶች ከዚህ ቀደም በማወቅም ይሀን ባለማወቅ በማኅበረሰቦች በሚደረግብን ጫና ወደፊት ሳንመጣ፣ ከወንዶች እኩል የእውቀት፣ የኢኮኖሚና የመሪነት ሥፍራ ሳይኖረን አብዛኞቻችን ጥቅማችንን አጥተናል፣ የኢኮኖሚ ጥገኛ በመሆን ኑሮን ለመግፋት ተገደናል››ም ብለዋል፡፡
ዛሬ የተፈጠረው ዲጂታል ዓለም ለሴቶች ጠቀሜታው የላቀና በቀላሉም በመጠቀም ኑሮን ለማሻሻል ቢያስችልም፣ በአንድ ቤት አባወራው ስልክ ካለው በቂ ነው በሚልና አማራጭና ዘመናዊ የስልክ ቀፎ ከመግዛት ጀምሮ ለዚያ አገልግሎት የሚሆነውን ወጪ አለመኖር ሴቶችን ከቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት እንዳላቀቃቸው አክለዋል፡፡
ዘመናዊ የስልክ ቀፎ ቢገዛም የአጠቃቀም ችግር መኖር፣ ለኢትዮጵያ ሴቶች ተብለው የተለያዩ አፕሊኬሽኖች (መተግበሪያዎች) አለመኖር፣ በሚዲያዎች መጠለፍና በእነዚህ ሚዲያዎች ተፅዕኖ በመውደቅ ከዲጂታሉ ዓለም ከሚገኘው ከፍተኛ ትሩፋት ተቋዳሽ እንዳልሆኑ ተናግረዋል፡፡
ይህንን ክፍተት ለመሙላት ድርጅታቸው 66 ዲጂታል ላይብረሪዎችን በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በመክፈት ላይ እንደሆነና ሴቶች ቢጠቀሙበት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አብራርተዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ከተለያዩ ክፍለ ከተሞች ለተውጣጡ በፅዳት ሥራ ላይ ለተሰማሩና ለተመረጡ 350 የፅዳት ሠራተኞች 3.12 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ስማርት ስልኮችን ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀንን (ማርች 8) ምክንያት በማድረግ በስጦታ አበርክተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ምን ያህል ሴቶች ዲጂታል ሚዲያውን እንደሚጠቀሙ ተጠቅመው ምን ያህሉ ኑሮዋቸውን እንዳሻሻሉ የተጠና ጥናት ባይኖርም፣ በዓለም ላይ ኢንተርኔት የሚጠቀሙ ሴቶች 57 ከመቶ ነው፡፡
በቅርቡ የተባበሩት መንግሥታት የሴቶችን የበይነ መረብ አጠቃቀም አስመልክቶ ባወጣው ይፋዊ ሪፖርት፣ ሴቶች በይነ መረብን ለመጠቀም ያላቸው ፍላጎት አነስተኛ መሆኑን ያሳያል፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በቀላሉ ለትንኮሳ ስለሚጋለጡ ነው፡፡
ለሴቶች ምቹ ሥራ መፍጠሪያና በቀላሉ ሕይወታቸውን የሚያሻሽሉበትና የሚማሩበት ዲጂታል ሚዲያ ትልቅ ዕድልን የፈጠረ ቢሆንም፣ የቴክኖሎጂው ፈጣሪ፣ አስተዳዳሪዎችና ተቆጣጣሪዎች ውስጥ የሴቶች ውክልና አነስተኛ መሆኑ ሌላው እንዳይጠቀሙ ከሚያደርጋቸው ሁኔታ ውስጥ ይጠቀሳል፡፡
እነዚህና ሌሎች ምክንያቶች ሴቶች የራሳቸውን የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ማጎልበት ብቻ ሳይሆን በቴክኖሎጂ የመለወጥ አቅማቸውን መገደቡም ተመልክቷል፡፡
ባለፉት አሥር ዓመታት ውስጥ ሴቶች ከዲጂታል ምኅዳሩ መገለላቸው፣ ዝቅተኛና መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት አንድ ትሪሊዮን ዶላር እንዲቀንስ ማድረጉን ሪፖርቱ ይናገራል፡፡
እ.ኤ.አ. ከ2019 ጀምሮ የተደረገ ዳሰሳ እንደሚያመለክተው፣ ሴቶች በይነመረብን የመጠቀም ሁኔታቸው በ20 ሚሊዮን ጨምሯል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ 63 በመቶ የበይነመረብ ተጠቃሚዎች ሴቶች ናቸው፡፡