- እኛ ሳንፈቅድ እንዴት ሊያቋቁሙ ቻሉ? ስምምነታችን እንደዚያ ነው እንዴ?
- በስምምነታችን መሠረትማ እኛ ሳንፈቅድ መቋቋም አይችልም። የእኛ ተወካዮችም በአባልነት መካተት አለባቸው።
- ታዲያ ምን እያደረገ ነው? ስምምነቱን መጣሳቸው ነው?
- ክቡር ሚኒስትር እነሱ እንደዚያ አላደርግንም፣ የፌዴራል መንግሥት ሳያጸድቀው የሽግግር መንግሥት አይመሠረትም እያሉ ነው።
- ታዲያ ምንድነው የሠሩት?
- ረቂቁን ነው የሠሩት።
- ረቂቅ ምን?
- ረቂቅ መንግሥት።
[ክቡር ሚኒስትሩ ከባልደረቦቻቸው ጋር ሆነው የከተማ አስተዳደሩን ኃላፊ እየገመገሙ ነው]
- ባለፈው በተገናኘንበት ወቅት የተለያዩ ማሳሰቢያዎችን ሰጥቼ ነበር።
- አዎ። ትክልል ነው ክቡር ሚኒስትር
- ለምሳሌ በሁሉም የከተማዋ ክፍሎች በ90 ቀን መፈጸም የሚችሉ ፕሮጀክቶች ተለይተው እንዲተገበሩ ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቼ ነበር።
- አዎ።
- እኮ ከምን ደረሰ?
- በሁሉም የከተማው ክፍሎች ተጀምሯል። በተለይ በአዲሱ ክፍለ ከተማ አመቺ ቦታ በመኖሩ የተለያዩ የ90 ቀን ፕሮጀክቶችን እየተገበርን እንገኛለን።
- ለምሳሌ ምን ተተገበረ?
- የጓሮ አትክልቶችና መመገቢያ ማዕከላትን አጠናቀናል በተጨማሪም የከብት ዕርባታ ፕሮጀክት…
- ከብት ዕርባታ በ90 ቀን?
- ከብቶቹ በ90 ቀን እንደማይደርሱ የተረዳነው ፕሮጀክቱን ከጀመርን በኋላ ነው።
- ስለዚህ ፕሮጀክቱ ታጠፈ?
- አልታጠፈም። መፍትሔ አበጅተንለታል።
- ምን አደረጋችሁ?
- የደረሱ ከብቶችን ለይተን አስገብተናል።
- ለምን የደረሱ?
- ለመታለብ።
- ማሳሰቢያ የሰጠሁት ግን ለአንድ ክፍለ ከተማ ብቻ አይደለም።
- ልክ ነው ክቡር ሚኒስትር።
- አመራሩ ቢሮ መዋልና በቪኤይት መንፈላሰስ ከዚህ በኋላ አይችልም። ፒክአፕ እየነዳ ፕሮጀክቶችን ይከታተል ብዬ ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥቼ እንዴት እስካሁን አይጀመርም?
- በማሳሰቢያው መሠረት የከተማ አመራሩ ቪኤይት እንዳይነዳ ከልክለን ጎን ለጎን የጀመርነውን ጨረታ ሰሞኑን አጠናቀናል።
- የምን ጨረታ?
- የፒክ አፕ።
- ምን?
- አመራሩ ፒክ አፕ እየነዳ ፕሮጀክቶችን እንዲከታተል በሰጡት ማሳሰቢያ መሠረት የተፈጸመ ነው።
- አመራርነት በቪኤይት መንፈላሰስ አይደለም ብል ፒክ አፕ ገዛችሁ?
- በግልጽ እኮ ነው የገዛነው?
- በግልጽ ማለት?
- በግልጽ ጨረታ።
- እሺ ሌላስ ምን ገዛችሁ?
- አመራሩ ፒክ አፕ ቢመደብለትም ቢሮ መዋሉን ሊተው ባለመቻሉ ይህንን የሚያስቀር ግዥ እንዲፈጸም ወስነናል።
- የምን ግዥ?
- ለእያንዳንዱ አመራር በደረጃው ልክ ዘመናዊ ላፕቶፕና ሞባይል ስልክ እንዲገዛ።
- ምን?
- አዎ። ከዚህ በኋላ ቢሮ ለመዋል ምክንያት አይኖራቸውም። ባሉበት ሆነው በስልካቸው ወይም በላፕቶፕ መገልገል ይችላሉ።
- እኔ ያልኩት ሕዝብ እንድታገለግሉና ቢያንስ የአቅመ ደካሞችን ቤት እንድታድሱ፣ እንድትጠግኑ እንጂ …
- ክቡር ሚኒስትር ስለእሱም ተወያይተን ወስኔ አሳልፈናል።
- ምን?
- አመራሩ የአቅመ ደካሞችን ቤት ለማደስ እንዲነሳሳ ይጠቅማል ያልነውን ወሳኔ አሳልፈናል።
- ምን ወሰናችሁ?
- ቤት ለሌለው አመራር ቤት እንዲሰጥ ቤት ላለው ደግሞ…
- እሺ… ቤት ላለው ምን?
- ቤቱን የሚያድስበት ወጪ በአስተዳደሩ እንዲሸፈን ወስነናል።
- ወሰናችሁ?
- አዎ። ከዚህ በኋላ የአቅመ ደካሞችን ቤት ላለማደስ ማቅማማት አይችሉም፣ ምክንያትም አይኖራቸውም።
- እኔም ሳላቅማማ አድሰዋለሁ!
- ምኑን?
- ካቢኔውን!
[የከተማ አስተዳደሩ ኃላፊ ከስብሰባው ከወጡ በኋላ ወደ ሚኒስትሩ ስልክ ደወሉ]
- ክቡር ሚኒስትር ቅድም የተናገሩት የምርዎትን እንዳልሆነ ተስፋ አደርጋለሁ?
- የሕዝብ ሀብት እየባከነ እንዴ እቀልዳለሁ?
- ክቡር ሚኒስትር ሀብት እያባከንን አይደለም።
- ታዲያ ሌላ ምን ሊባል ነው?
- ቅድም ብቻዎትን ስላልነበሩ ተቆጥቤ እንጂ ምክንያቱ ሌላ ነው።
- ሌላው ምክንያት ምንድነው?
- ክቡር ሚኒስትር እኔ ፍርኃት አለኝ፣ ሥጋት አለኝ!
- የምን ሥጋት?
- አመራሩ ልቡ ሸፍቷል የት ቦታ እንደቆመ አይታወቅም። ይኼ አስፈርቶኛል።
- ስለዚህ?
- ሥጋት ስላለኝ ነው ፈጥኜ እስከ ወረዳ ያለውን አመራር በጥቅማ ጥቅም ለመያዝ የወሰንኩት።
- እንደዚያ ነው?
- አዎ። ፍርኃት ስላለኝ ነው። ሥጋት አለኝ።
- እንደዚያ ከሆነ ገብቶታል ማለት ነው።
- ምኑ?
- ፕሮጀክቱ።
- የቱ ፕሮጀክት?
- የ90 ቀን!