በዓድዋ ከ127 ዓመታት በፊት በተካሄደውና ኢትዮጵያ ጣሊያንን ድል ላደረገችበት ለታሪካዊው የዓድዋ ጦርነት መነሻ በመሆን ከሚጠቀሱ ምክንያቶች መካከል ከ134 ዓመታት በፊት የተደረገው የውጫሌ ውል ቀዳሚው ነው፡፡ የውጫሌ ውል በዳግማዊ አፄ ምኒልክና በጣሊያን ንጉሥ ኡምቤርቶ ወኪል ኮንት አንቶሎኒ መካከል ወረኢሉ ቦሩ ሜዳ አካባቢ ውጫሌ በሚባል ቦታ ሚያዝያ 25 ቀን 1881 ዓ.ም. የተደረገ ውል ነው፡፡
ጣሊያን የውጫሌ ውል የንግድና የፍቅር ነው በማለት ብትቀርብም ከመነሻው ጀምሮ ብዙ ጥርጣሬ፣ ክርክርና ተቃውሞ በኢትዮጵያውያን ዘንድ ሲሰማ እንደነበር ታሪክ ያስታውሳል፡፡ በተለይ በአንቀጽ 17 ምክንያት የተነሳው ተቃውሞ በቀጥታ በሁለቱ አገሮች መካከል ለተካሄደው ጦርነት መነሻ እንደሆነ ይታመናል፡፡
በአንቀጽ 17 አማካይነት ጣሊያን አምታች የሆነ ቃል በመጠቀም የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በመገርሰስ የጣልያን ሞግዚት እንድትሆን ቀዳዳ እያበጀች መሆኑ ሲታወቅ እቴጌ ጣይቱ ‹‹እኔ ሴት ነኝ፣ ጦርነት አልወድም፡፡ ግን እንዲህ መሳዩን ውል ከምቀበል ጦርነት እመርጣለሁ ይስሙ ንጉሥ!›› የሚል ኃይለ ቃል አሰምተዋል፡፡ ይኼን ንግግራቸውን ተከትሎም የውጫሌ ውል የተፈረመበት ቦታ ይስማ ንጉሥ በሚል ተሰይሞ እዚህ ዘመን ደርሷል፡፡
ይህን ታሪካዊ ሁነት የሚዘክር የንጉሠ ነገሥቱ ዳግማዊ አፄ ምኒልክና የእቴጌ ጣይቱ ሐውልቶች በይስማ ንጉሥ የተተከሉ ሲሆን፣ በዘንድሮው የዓድዋ ድል በዓል አጋጣሚ ለምረቃና ለሕዝብ ዕይታ በቅተዋል፡፡
አሚኮ እንደዘገበው፣ የንጉሡ ነገሥቱና የንግሥቷ ሐውልት የውጫሌ ውልን የሚያስታውስ፣ ዓድዋን የሚያስብና ታሪካቸውን የሚዘክር ነው። ሐውልቱ በውጫሌ ውል አንቀጽ 17 ላይ በነበረው ክርክር በዙፋን ላይ ተቀምጠው ሲወያዩ፣ እቴጌ ጣይቱ በብስጭት ተነስተው ውሉን ሲቃወሙ የሚያሳይ ነው። እቴጌዋ ከዙፋናቸው ሲነሱና ዳግማዊ ምኒልክ በዙፋናቸው እንደተቀመጡ ያሳያል።
የውጫሌን ውል በማፍረስ፣ የአገራቸውን ሕዝብ በሰላ ጥበብ በመምራት በዓድዋ ላይ ድል ያደረጉት ዳግማዊ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ ዓድዋ በተነሳ ቁጥር ይታወሳሉ ያሉት
የደቡብ ወሎ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ መስፍን መኰንን፣ የዓድዋው ጦርነት የውጫሌ ውልና የቅኝ አገዛዝን በመቃወም የተደረገ ጦርነት መሆኑን ተናግረዋል።
‹‹ኢትዮጵያውያን ሰውነትን መነሻ አድርገው ነጭና ጥቁር እኩል፣ ነጭ ከጥቁር አይበልጥም በማለት ያደረጉት ጦርነትም ነው፤›› ብለዋል።
በውጫሌ ውል ዙሪያ ክርክር ሲደረግ እቴጌ ጣይቱ ‹‹ንጉሥ ሆይ ይስሙ›› ብለው የውጫሌን ውል ተቃወሙ። ያም ንግግራቸው የስም ስያሜ ሆኖ ይስማ ንጉሥ እየተባለ አሁንም ይጠራል ነው ያሉት።
ያን ታሪክ የሚዘክር ስምና ሙዚየም በውጫሌ ከአምባሰል ተራራ ግርጌ ይገኛል። ከንጉሡና ከንግሥቲቱ ሐውልት ዙሪያ የዚያን ዘመን ታሪክ ሊያስታውስ የሚችሉ ሌሎች ሐውልቶችም ይቆማሉ ብሏል የአሚኮ ዘገባ።
ሐውልቶቹን መርቀው ለዕይታ ክፍት ያደረጉት የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) እና የአማራ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ምክትል ቢሮ ኃላፊ ህሊና መብራቱ ናቸው።
ሃቻምና ለዓድዋ ጦርነት ምክንያት የሆነውና የውጫሌ ውል በተፈረመበት ታሪካዊ ቦታ ላይ የተሠራው የይስማ ንጉሥ ሙዚየም ጥር 6 ቀን 2013 ዓ.ም. ለምረቃ መብቃቱ ይታወሳል፡፡
የሙዚየሙ የመግቢያ በር የኢትዮጵያ ቁጥር ፲፯ (17) አምሳል የተገነባ ሲሆን፣ የባህል ማዕከሉ የኢትዮጵያን ታሪክ የሚያሳዩ መረጃዎችን ያካተተ ነው፡፡ የቀለም ቅቡም የአሸናፊነትና የተሸናፊነትን እንዲወክል ተደርጎ የተዘጋጀ ሲሆን፣ በማዕከሉ ጣሪያ ላይ የአሸናፊነትን የሚያመለክት የእጅ ምልክት ተሠርቷል፡፡
የአምባሰል ወረዳ ሙዚየሙ በተመረቀበት ጊዜ በድረ ገጹ እንደገለጸው፣ የባህል ሙዚየሙ፣ ቢሮዎችና ካፌን አካቶ የተሠራበት የይስማ ንጉሥ የባህል ማዕከል፣ የአካባቢውን ባህል ለማስተዋወቅ አገራዊ ፍቅርና አንድነትን ለማስተማር፣ ታሪክን ለማስረዳትና ለቀጣይ ትውልድ ጠብቆ ለማቆየት የጎላ ሚና እንዲኖረው ታስቦ ተገንብቷል፡፡
ከውጫሌ ውል እስከ ዓድዋ ድል የኢትዮጵያ ታሪክን ሊገልጽ በሚችል መልኩ የተደራጀው ማዕከሉ በተለይም የጥቁሮችን የአሸናፊነት መንፈስ የሚያንጸባርቁ ይዘቶች አሉት፡፡
በእነዚህ ጊዜያት የነበሩና የኢትዮጵያ ታሪክን የሚገልጹ ታሪካዊ ቅርሶችን ከፌዴራሉና ከክልሉ መንግሥታት እንዲሁም በስጦታ፣ በውሰት፣ በግዥና በውርስ መልኩ በማኅበረሰቡ እጅ የሚገኙ ልዩ ልዩ ቅርሶችን ሰብስቦ ወደ ሙዚየሙ እያስገባ መሆኑም ተገልጿል፡፡