የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ማግሥትና በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት፣ በፓርቲው አመራሮች መካከል ተፈጥሮ የነበረውን አለመግባባት በውይይትና በሽምግልና በመፍታት፣ ለተሻለ ትግል ተዘጋጅቻለሁ ሲል አስታወቀ፡፡
የአብን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጣሂር መሐመድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ፓርቲው ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በአማራ ሕዝብ ላይ የሚታዩ የሥርዓትና ሰው ሠራሽ ችግሮችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲወገዱ፣ የአማራ ብሔርተኝነትን እንደ አንድ የመታገያ መንገድ አድርጎ ኢትዮጵያዊነትን ማፅናት በሚል ሲሠራ ቆይቷል፡፡
ይሁን እንጂ በስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ማግሥት፣ በተለይ ደግሞ ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ጋር ተያይዞ የተፈጠሩ የፓርቲ የውስጥ ችግሮች፣ ከቀን ወደ ቀን እየሰፉ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡
‹‹እጅግ ፈጣንና ተለዋዋጭ በሆነው የኢትዮጵያ ፖለቲካ እነዚህን ችግሮች ወዲያውኑ አለመፍታት፣ በየቀኑ ችግር ውስጥ ለሚወድቀው ሕዝባችን ድምፅ ሆኖ አንድ ላይ ለመሥራት በጣም ፈታኝ ሆኖ ቆይቷል፤›› ብለዋል፡፡
አብን ከዚህ ችግር ውስጥ ለመውጣት በአንድ ጀንበር ብቻ ሳይሆን ለረዥም ጊዜያት ንግግርና ውይይት ሲደርግ ቆይቶ፣ በውስጡ የተፈጠሩ አለመግባባቶችን አንዳንዶቹን በጊዜ ሒደት በማረምና በአመራሩ ውስጥ የነበረውን አለመግባባት በውይይትና በሽምግልና መፍታት መቻሉን አቶ ጣሂር ተናግረዋል፡፡
ፓርቲው አሁን ካለው አገራዊ ሁኔታ አንፃር፣ በተሻለ ለሕዝብ ድምፅ የሚሆንበትና የተጠናከረ ትግል የሚያደርግበት ወሳኝ የታሪክ ዕጣ ፈንታው ነው ብሎ እንደሚያስብ አቶ ጣሂር ገልጸዋል፡፡
‹‹በቅርብ ጊዜያት ሕወሓትና የትግራይ የፖለቲካ ዘዋሪዎች በአማራ ሕዝብ ላይ በቋሚነት የያዙት አቋም መስተካከል እስካልቻለ ድረስ፣ ሕዝባችን አደጋ ላይ መሆኑን ቅስቀሳ በማድረግ በከፍተኛ ሁኔታ ለመሥራት ሕዝባችን አደራጅተን ተንቀሳቅሰናል፤›› ሲሉ አክዋል፡፡
‹‹በአሁኑ ወቅት ደግሞ በኦሮሞ የፖለቲካ ኃይሎች መረን የለቀቁ አንዳንድ እንቅስቃሴዎች መታረም እንዳለባቸው ገልጸው፣ ለጋራ አገር ግንባታው መስተካከል ሲባል ትግል ያስፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ከዚህ ባለፈ ብልፅግና ፓርቲ አንድ ወጥ አለመሆኑን ጠቅሰው፣ የትናንቱ የ27 ዓመታት የጨለማ ዘመን በማረም ወደ አንድነት እመጣለሁ ብሎ ሲንቀሳቀስ፣ እኛም እንደ ፓርቲ እንዲህ ዓይነት ለውጦች ካሉ መተጋገዝ እንችላለን ብለን አቋም የወሰድንባቸው ሒደቶች ሊስተካከሉ አልቻሉም፤›› ብለዋል፡፡
ስለዚህ ያንን ለማስተካከል አሁንም ተጨማሪ ትግሎች እንደሚያስፈልጉ ጠቅሰው፣ የትኩረት አቅጣጫዎቻቸው ሥልጣን በያዘው አካል ላይ መሆኑን ለይተናል በማለት አስረድተዋል፡፡
አብን በቀጣይ አዲስ መንገድ፣ ስትራቴጂና መናበብ የሚፈልጉ ነገሮች እንደሚያስፈልጉ መገምገሙን የገለጹት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው፣ እነዚህን ጉዳዮች በማስተካከል ወቅታዊ ሁኔታውን በሚገባ አንብቦ የኃይል አሠላለፍ ሊቀያየር እንደሚችልና ይህ አሠላለፍ ባለፈው ጊዜ ከተሄደበት አኳያ እየተገመገመ አዳዲስ አጋር አካላትንም በማሰባስብ እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡