በትራፊክ አደጋ ምክንያት በ2015 ዓ.ም. በስድስት ወራት 1,872 ሰዎች መሞታቸውንና ይህም ከ2014 ግማሽ ዓመት ጋር ሲነፃፀር 7.5 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን የመንገድ ደኅንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት አስታወቀ፡፡
በ2015 በስድስት ወራት የደረሰው የትራፊክ አደጋ 23,280 መሆኑን፣ ከ2014 ዓ.ም. ስድስት ወራት ጋር ሲነፃፀር የ2,918 ወይም 14.3 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን የመንገድ ደኅንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ገልጿል፡፡
በተያዘው በጀት ዓመት ስድስት ወራት ብቻ 2,888 ከባድ የአካል ጉዳትና 2,398 ቀላል የአካል ጉዳት መድረሱን፣ የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ፈቲያ ዳድገባ ተናግረዋል፡፡
በትራፊክ አደጋ የደረሰው የንብረት ውድመት በግማሽ ዓመቱ ቅናሽ ማሳየቱን ገልጸው፣ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ሦስት በመቶ ያህል ቀንሷል ብለዋል፡፡
በ2014 ዓ.ም. 1,550,946,327 ብር የሚገመት ንብረት በትራፊክ አደጋ መውደሙን ያስታወሱት ወ/ሮ ፈቲያ፣ በዘንድሮ በተመሳሳይ ወቅት 1,504,417,980 ብር ያህል ንበረት መውደሙን፣ ከዓምና ከተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ደግሞ በሦስት በመቶ መቀነሱን ገልጸዋል፡፡
እንደ ወ/ሮ ፊቲያ ገለጻ፣ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የሕግ ማሻሻያዎች ይገኙበታል ብለዋል፡፡
የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ ደንብ ቁጥር 208/2003 እና 393/2009 ለመሻር የተዘጋጀ ረቂቅ ሰነድ፣ የፍጥነት ወሰን መለኪያ ደንብ ቁጥር 492/2014 ማሻሻያ ረቂቅ ሰነድ የትራፊክ አደጋን ለመቀሰን እየተዘጋጁ ከሚገኙ መካከል ይጠቀሳሉ ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ችግሩን ለመቅረፍ ቁጥጥር በተደረገባቸው 26 የፍጥነት ዓይነቶች 99,306 አሽከርካሪዎች ጥፋት ፈጽመው መገኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
ከተፈቀደላቸውት ክብደት በላይ (ትርፍ ሰው የጫኑ) 19.36 በመቶ፣ በተከለከለ ቦታ መቆም 17.31 በመቶ፣ ከፍጥነት በላይ ማሽከርከር 14.42 በመቶ ጥፋተኛ ሆነው መገኘታቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስረድተዋል፡፡
የደኅንነት ቀበቶ ያላሰሩ 10.59 በመቶ፣ ስልክ እያወሩ ያሽከረከሩ ስምንት በመቶ፣ ሦስተኛ ወገን ካልለጠፉ ደግሞ 694 ውስጥ 356 አሽከርካሪዎች በገንዘብ ተቀጥተው ወደ ኢንሹራንስ እንደገቡ፣ የተቀሩት 338 አሽከርካሪዎች ክስ እንደተመሠረተባቸው ተገልጿል፡፡
ችግሩን በዘለቄታ ለመፍታት በሁሉም ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር፣ ከየካቲት 24 ቀን እስከ መጋቢት 23 ቀን 2015 ዓ.ም. ድረስ ይከናወናል ተብሏል፡፡